Skip to main content

ነገረ አማት ወምራት


ነገረ አማት ወምራት

ትርጉም፦
የባል እናትና አባት ለሚስት ዐማቶች ናቸው። አንዱን ከሌላው ለመለየት የወንድ አማቷ ወይም የሴት አማቷ ይባላሉ። የሚስት አባትና እናትም ለባል ዐማቶቹ ይባላሉ። የወንድ አማቱ ወይም የሴት አማቱ ተብለው ይለያሉ። በዚህ ጽሑፍ አማት ሲባል የባል እናትን ፥ ምራት ሲባል ደግሞ የልጁ ሚስትን ማለት ነው።
አዋጅ፦
ጊዜ ወስጄ ያጠናቀርሁት ነው።ዐላማዬም በጉዳዩ በቤተክርስትያን ውይይት ለማነቃቃትና ለዚሁ መነሻ ዐሳብ ለማቅረብ ነው። ይህ ለመግቢያ ይሁን።  በአማትና ሥነ-ሥርዐት (awondimts.com)
 ይቀጥላል። (ዋቢ መጨረሻ ተዘርዝሯል)

ነገረ አማት ወምራት
    ልጆች ማንነታቸውን የሚመሠርቱበት፣ የወገንነት ስሜት የሚያገኙበት፣ ለራሳቸውም ሆነ ለወገኖቻቸው የሚኖራቸውን ኅላፊነት የሚማሩበት ማኅጸን ቤተሰብ ይባላል። ደህንነት፣ ከለላ ፣ ድጋፍና ፍቅር አግኝተው የሚያድጉትም በዚያ ነው። ቤተሰብ የሚሰፋውና ቀጣይ የሚሆነው ደግሞ በጋብቻ /በትዳር ነው። ትዳር ማለት በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መኻል አዲስን ቤተሰብ ለመመሥረት የሚገባ ቃልኪዳን ነው። ከዚህ የተለየ ትርጉም የሚሰጡት ማኅበረሰቦች መኖራቸው የሚታወቅ ሲሆን ይህ ጽሑፍ በዚሁ ክርስትያናዊ ትርጉም የተወሰነ ነው።
    ትዳር በወላጅ ወይም በተጋቢዎቹ በራሳቸው ምርጫ ሊመሠረት ይችላል። በወላጅ ምርጫ የሚፈጸሙ በሃይማኖትና በማኅበራዊ አቋም በሚኳኋኑ መኻል ይገደባል ወላጆች ሲሆኑ ጥሩ የቤተሰብ ዳራ ፣ በቂ መተዳደሪያ እንዲሁም በተመሳሳይ ሃይማኖት ወይም ዘር መሆናቸውን አረጋግጠው ይድራሉ።የሚመራረጡት ወላጆች ነበሩ።
በተጋቢዎቹ በራሳቸው ምርጫ ትዳር ሲመሠረት ግን ወላጆች በምርጫው ላይ የሚያሳድሩት ተጽእኖ እስከማይኖር ይደርሳል። ጋብቻዎቻቸውን የመመረጥ እድል አይኖራቸውም። ተከፉም ተደሰቱም ልጆቻቸው ከመረጡላቸው ጋር መዛመድ ግዴታቸው ይሆናል
    ለአቅመ አዳም/ሔዋን የደረሱ በራሳቸው ሲመራረጡ በማንኛውም ዕድሜያቸው ይሆናል። የአስተዳደግ፣ የማኅበራዊ አቋም የሃይማኖት ልዩነት ሊኖራቸው ይችላል። የሀብት፣ የትምህርት ደረጃ መበላለጥ እንዲኖራቸውም በሩ ክፍት ነው። ከዚህ የተነሳ የአማትና የምራት ግንኙነታቸው በወላጆች ምርጫ ከሚጠበቀው ይልቅ የበለጠ መቃቃር የሚታይበት የመሆን ዕድል አለው ለዚህም ምክንያቱ አማትና ምራት ከተለያየ ጎሳ ወይም ሃይማኖት የተገኙ ሲሆኑ በተለይ የልጅ ልጆች አስተዳደግን በተመለከተ ልዩነቱ የሰፋ ስለሚሆን ነው።
    በየትኛውም ልማድ ጋብቻው ይመሥረት አዲሶቹ ተጋቢዎቹ ቢያንስ የሦስት ቤተሰብ አባላት ይሆናሉ። ራሳቸው የመሠረቱት የአዲሱ ቤተሰብ እንዲሁም የተገኙባቸው ሁለቱ የወላጆቻቸው ቤተሰቦች (አባት፣ እናት፣ ወንድምና እህት) ማለት ነው። ስለዚህ ትዳርን የሁለት ቤተሰብ መዋሐድ አድርጎ ማየትም ይቻላል። እንደ አፍሪካውያን ከሆነ ደግሞ የሁለቱ ቤተሰብና ከአብራካቸው የተከፈሉ ልጆቻቸው ብቻ ሳይሆን ከአንድ የጋራ ቅድመ አያት የተገኙ ዝርያ ሁሉ እንደ ቤተሰብ ተደርገው ይወሰዳሉ።በእርግጥ የሁሉም የዝምድና ቅርበት እኩል ተደርጎ አይታይም።
    በምርጫቸው የሚጋቡ ግንኙነቱ የባልና ሚስቱ መጣመር ብቻ አድርገው ይቆጥሩታል። ከባል ቤተሰብና ከሚስት ቤተሰብ ጋርም መያያዝ መኖሩን ልብ አይሉትም።ከዚህም የተነሳ አማቶች ጠቃሚ ሚና እንደሚኖራቸው አይገነዘቡም።ይህ ደግሞ ከአጀማምሩ ግንኙነቱን ችግር ያለበት ያደርገዋል።
    ለነገሩ በየትኛውም መንገድ የተመሠረተ ጋብቻ በጅማሮው ዘመን ላይ ድንግርግር (ሚናን ለመለየት ማስቸገሩ) ማለቱ አይቀርም። በግንኙነትም  የመግባቢያው ዘዴ ግራ ያጋባል። ነጻ በመሆንና በወላጆች በመደገፍ መኻል ሚዛኑን እስኪያገኙት ድረስ ይኸ ችግር አይቃለልም።መቀራረቡ እየተጓተተ ሄዶ በመኻሉ ምራት ልጅ ከወለደች መራራቁ ሊባባስም ይችላል
    የግንኙነቱ ድንግርግር የሚነሳው ከሦስቱ ቤተሰቦች መገናኘት ምክንያት ነው። ያገናኛቸው ደግሞ ባል/ልጅ ነው። ያ ባይሆን የሚያዳርሳቸው ነገር ባልኖረም።የድንግርሩ መነሻ የሥልጣን ትግል (የማን ዐሳብ ይሰማ)  ፣ የታማኝነት ጉዳይ ወይም ከወላጆች ተጽዕኖ ነጻ የመሆን እንዲሁም በሕይወት የሚደርሱ መጨናናቆች ሊሆኑ ይችላሉ።
    በአፍሪካውያን የተደረገ አንድ ጥናትም ከዚሁ ጋር የሚቀራረቡ አምስት ነጥቦችን ይዘረዝራል።
  1. ቅርበትን መፈለግ፦ ከአብራክ የተወለደ ብቻ ነው ከልብ መወደድ የሚቻለው በሚል ፈሊጥ የሌላውን ልጅነት ባለመቀበል የራስን ልጅ ብቻ ለይቶ መውደድና ሌላውን ቸል ማለት
  2. አማቶችን ከቤተሰቡ አለማዋሐድ፦ወላጆች በልጆቻቸው ላይ ብዙ ደክመዋልና በአዲሱ ቤተሰብ በመልካም እንዲስተናገዱ (ፊት እንዳይነሱ) ይጠብቃሉ።
  3. ወላጆች ሚና እንዲኖራቸው አለማድረግ፦ይኼ ጭራሽኑ በልጃቸው ቤት ገብተው አመራር ለመስጠት እስከመፈለግ ሊያነሳሳቸው ይችላል
  4. ምራቶች ሥጋት ሲገባቸው፦በአማቶች እንዳልተወደዱ (ብቁ አይደላችሁም እንደተባሉ ሲሰማቸው) እስከ መበጥበጥ ይደርሳሉ፡፡ለምሳሌ ልጅ ሳይወልዱ ሲቀሩ
  5. ድንበር ያለፈ የወላጅ ተጽዕኖ፦ በአፍሪካ አንዳንድ ወላጆች ያበዙታል።የልጆቹን ቤት ሙሉ ለሙሉ ልቆጣጠር ይላሉ። ትርፉ የልጆቹ ሃዘን ምናልባትም የትዳሩ መፍረስ ነው
በእርግጥ በአፍሪካ አማቶች በቤተሰብ እድገት ቁልፍ ሚና ይጫወታሉ። ልጆቻቸውን በትዳር እንዴት ውጤታማ እንዲሆኑ ይመክራሉ፣ የልጅ ልጅን በመንከባከብ ይረዳሉ። ታዛዥና ትሁት ለሆኑ (ያገቡ ልጆቻቸው) መልካም ነገር ሊያደርጉላቸውም ይችላሉ። የማይታዘዙት ግን የአማቶች ቅጣት ያገኛቸዋል። ይህ ልማድ ድንበር ማለፍን አያስከትልም ትላላችሁ?
    ይህ ይባል እንጂ  የሁሉ አማትና ምራት ግንኙነት በተረት እንደሚነገረው፣ በቀልድ እንደሚያስቀው፣ በዘፈን እንደሚያሳዝነው የጠለሸ አይደለም። እርስ በእርስ የሚዋደዱና መልካም ግንኙነት ያላቸው አሉ። ፍርሃት የከበበውና ጎምዛዛ ግንኙነት ያላቸውም አይጠፉም። አዎ! መወዛገብ የመላበትና ትዳርን የሚጎዳ ሊኖር መቻሉም አያጠያይቅም። በአመዛኙ ግን መኻከለኛ ሆኖ ወደ ጥሩነት ያዘነበለ ሆኖ ይገኛል ። ምናልባት ቢጠና (ተጠንቶም እንደሆን አላወቅሁም) የኢትዮጵያውያንም ተመሳሳይ ይሆናል። መቼም የኢትዮጵያ አማቶች እንደ ሕንድ አማቶች አይሆኑም የሚል የዚህ ጸሐፊ ግምት አለ። አሁን መሻሻል እያሳየ ቢሆንም በሕንድ አገር ምራት ሙሉ ለሙሉ በአማቷ ቁጥጥር ሥር ትኖራለች። ለሕክምና ወደ ጤና ድርጅት እንኳ ብቻዋን እንድትሄድ አማት አትፈቅድላትም።
    በሚስትና በእናቷ መኻል እንዲሁም በባልና በሚስት ወላጆች መኻል ውጥረት ሊኖር ቢችልም ጥናቶች እንደሚያሳዩት ቅድሚያ ተከሳሽ አማት (የባል እናት) ስትሆን ለጣቂዋ ምራት (የልጁ ሚስት) ናቸው።በባልና በሚስት ወላጆች መኻል ውጥረት የሚኖረውም በአመዛኙ  በትዳሩ ጣልቃ የሚገቡ   ሆኖ  ሲሰማው ነው።
    በአማትና በምራት መኻል ግንኙነቱን ሰላማዊ ቢያደርጉ የመጀመሪያ ተጠቃሚዎች እነርሱ ራሳቸው ይሆናሉ። አማት ከልጇ ጋር መገናኘት፣ የልጅ ልጆቿን አግኝታ አብራ ጊዜ እንድታሳል፣ ፍቅርን እንድትለዋወጥ፣ ስታረጅም እንድትጦር ይረዳታል  ። ለምራት ደግሞ ከውኃ አጣጭ ጋር ያለውን ግንኙነት በጎ ያደርግላታል ። ልጆቿን በመንከባከቡ እርዳታ ታገኛለች፣ የገንዘብ አቅም ካላቸው በዚያም በኩል ርዳታ ልታገኝ ትችላለች። እርሷም በተራዋ አማት ስትሆን የሚረዳትን ንድፍ ታገኝበታለች ። እናት የሞተባት ወይም የእናት ፍቅር ያላገኘች ደግሞ ያንን ጉድለቷን ልትሞላላት ትችላለች።
    ሴቶች ማኅበራዊ ግንኙነትን በመምራቱ ዋና ተዋናይ እንደመሆናቸው መጠን የሁለቱ ግንኙነት የቤተዘመዱን መተሳሰር ይወስነዋል ። መተባበሩ ወይም መከፋፋቱ ለምራትና ለአማት ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይሆንም። ለሦስቱም ቤተሰቦችና ባጠቃላይ በጋብቻ ለሚዛመዱት ሰፊ ማኅበረሰብ የመትረፍ ዕድል አለው። ማኅበረሰቡ ላለበት ቤተክርስቲያንም አይደርስም አይባልም። ስለዚህ ቤተክርስቲያን ለዚህም ጉዳይ ትኩረት ልትሰጥ ያስፈልጋታል።የንግድና መሰል የሥራ ሽርክና በቤተሰብ መኻል ሲኖርም የአማትና የምራት ግንኙነቱ እንደ አገባቡ አዎንታዊ ወይም አሉታዊ ተጽዕኖ ሊኖረው ይችላል። ይኸንን “በቀንድ ከብት ልማት” በተሠማሩ የተደረገውን አንድ ጥናት መሠረት አድርጎ መገመት ይቻላል።እንደተጋቡ ቅድሚያ ታማኝነታቸው ለመሠረቱት ለራሳቸው ቤት መሆኑን ማረጋገጡ የአማት-ምራት ችግርን ለመቅረፍ ዐይነተኛ መፍትሔ ነው።
    የአማትና ምራት ጉዳይ አትድረስብኝ-አልደርስባትም ማለት የሚቻልበት አይደለም። ለሁለቱም መገናኘት ምክንያት የሆነው ልጁ/ባሉ በመኻከላቸው እስካለ ድረስ ሊዳረሱ የሚችሉበትና ሊጋጩ የሚችሉባቸው አጋጣሚዎች ብዙ ናቸው።
ደግነቱ ከግጭት የመራቅ አቅጣጫም አለ።ምራት በእናትና በልጁ መኻል በተፈጥሮ (በመውለድ/በመወለድ)፣ አብሮ ታሪክን በመካፈል ውስብስብና የማይበጠስ የነገረ ልቡና ግንኙነት እንዳለ መገንዘብ ያሻታል። የአማትን ጥበቧን፣ ልምዷን ፣ጠቃሚነቷንና ሥጋቷን ልብ ማለት አማትን ሰላማዊ ያደርጋታል። አማት ደግሞ ለልጇ የአካልና የስሜት ፍላጎቱን ለቀሪው ዘመኑ ሁሉ የምትሞላለት፣በልጁ ሕይወት ዋናዋ ሴት ተዋናይ መሆኗን በመቀበል ከምራት ጋር ከመፎካከርና እርሷን በነገር ከመንካት ትራቅ።ሁለቱም ባልን በእናቱና በሚስቱ መኻል እንዲመርጥ የሚያስገድድ ሁኔታ ውስጥ አያስገቡት።አንደኛዋን እንዲመርጥ ሲገደድ ባልተመረጠችው ላይ ጉዳትና ቁጣ ያስከትላልና። ልጅ/ባልም ቢሆን አይፋዘዝ፣ እናቱን ያላገለላት (ያልረሳት) እንደሆነ እንዲሰማት በማድረግ ቅርበቱን/ቅድሚያ ታማኝነቱን ከሚስቱ ጋር ማድረግን ይማር።
ይህን በመግቢያነት ካተትኩ በኋላ ’ሪይል ሲምፕል’ የተሰኘ መጽሔት ካቀናበረው የተወሰደ የአማትና ምራት ግንኙነትን የሚያሳየውንና ሰላማዊ የማድረጊያ ስልቱን የሚያስረዳውን ጽሑፍ አቀርባለሁ። ጌታ ቢፈቅድ ብኖርም በሌላ ጊዜ ደግሞ ታሪኮቻቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ስለሚገኙ አማትና ምራት እጽፋለሁ።
እናንተን ክፉ አይንካብኝ!
ቸር እንሰንብት

ዋቢ 

ATTITUDE OF MOTHER-IN-LAW TOWARDS DAUGHTER-IN-LAW AS A DETERMINANT FAC... (iproject.com.ng)

 Curse of the Mummy-ji: The Influence of Mothers-in-Law on Women in India*Final_Manuscript.pdf (bu.edu)

Extending the Extended Family: The Mother-in-Law and Daughter-in-Law Relationship of Black Women on JSTOR

 Lopata, H. Z. (1999). In-laws and the concept of family. Marriage and Family Review, 28(3/4), 161-172.

Duvall, E. M. (1954). In-laws, pro and con: An original study of inter-personal relations. New York: Association Press

Allendorf, K. (2017). Like her own: Ideals and experiences of the mother-in-law/daughter-in-law relationship. Journal of Family Issues, 38, 2102–2127.

 Rittenour, C. E., & Kellas, J. K. (2015). Making sense of hurtful mother-in-law messages: Applying Attribution Theory to the in-law triad. Communication Quarterly, 63(1), 62-80. doi:10.1080/01463373.2014.965837

Fischer, L. R. (1983). Mothers and mothers-in-law. Journal of Marriage and Family, 45, 187–192

Michael E. Woolley and Geoffrey L. GreifAyers, J.D., Krems, J.A., Hess, N. et al. Mother-in-Law Daughter-in-Law Conflict: an Evolutionary Perspective and Report of Empirical Data from the USA. Evolutionary Psychological Science 8, 56–71 (2022). https://doi.org/10.1007/s40806-021-00312-x

 Mother-in-Law Problems: They're Worse for Women - TIME

Mother-in-Law Reports of Closeness to Daughter-in-Law: The Determinant Triangle with the Son and Husband Michael E. Woolley and Geoffrey L. Greif

 (Apostolou, 2015a, Perriloux et al., 2011).*Parent–Offspring Conflict Over Mating (sagepub.com)

Prentice, C. M. (2005). 

The assimilation of in-laws: The impact of newcomers on the structuration of families, Unpublished PhD thesis. Columbia: University of Missouri-Columbia. 

https://www.researchgate.net/publication/365803786_The_Bible_In-Laws_and_Family_in_Africa

 (Patterson, 1978).*5448-12959-1-PB.pdf Patterson, R. P. (1978). African Studies Curriculum Unit: The Cycle of Life in the African Family. USA: Illinois Univ. Retrieved October 23, 2022, from 

https://files.eric.ed.gov/fulltext/ED189006.pdf

 Silverstein, J. L. (1990). The problem with in-laws. Journal of Family Therapy, 14, 399–412. 



 


(



Comments

Popular posts from this blog

Comparative Theology የነገረ መለኮት ንጽጽር (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት)/ በብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ሲኖዳ ሳልሳዊ

 የነገረ መለኮት ንጽጽር  (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት): የወደደ  ሁሉ በነጻ እንዲጠቀምበት ተፖስቷል። ይሁን እንጂ መብቱ በሕግ የተጠበቀ ስለሆነ በየትኛውም መልኩ ለንግድ እንዲውል አልተፈቀድም። ልዩ ልዩ መግቢያ የሚለውን መጀመሪያ ካነበቡ በኋላ የተቀረውን በተመረጠው ቅደም ተከተል ማንበብ ይቻላል። ልዩ ልዩ መግቢያ   ጥምቀት   ትውፊት (ወግና ልማድ)   መካከለኝነት   ጾም የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ መንፈሳዊ ስጦታዎችና በልሳኖች የመናገር ስጦታ   ሥርዐት ንስሐ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ (1)  ድንግል ማርያምን ስለማክበር (2) ለጥያቄዎች መልስ (ሀ) ድንግሊትን ‘የወይን ግንድ (ተክል)’ና የ ‘ሕይወት በር’ የሚል ማዕረግ  ለምን እንሰጣታለን? (ለ) ወደ ድንግል ማርያም መጸለይ ትክክል ነው ወይ? (3) የድንግል ማርያም ድንግልና ዘላለማዊነት (4) ለተቃራኒ አስተያየቶች መልስ (ሀ) “የመጀመሪያ ልጇን” የሚለው ሐረግ (ለ) “ሚስትህ” የሚለው ሐረግ (ሐ) “አብረው ከመሆናቸው በፊት ጸንሳ ተገኘች” (መ) “የመጀመሪያ ልጇን እስክትወልድ አላወቃትም” (ሠ)  “ወንድሞቹ” የሚለው ሐረግ   የቅድስት ድንግል ማርያም  ክብሯ (1) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ድንግል እመቤታችንን አያከብሩም፤ ደግሞም እንድታማልድላቸውም (እንድትማልድላቸውም)  አይጠይቋትም።ከእነርሱ ወገኖች አንዳንዶቹ እንዲያውም ጫጩቱ ከተፈለፈለ በኋላ ዋጋ ከሌለው የዶሮ እንቁላል ቅርፊት ጋር እስከሚያመሳስሏት ይደርሳሉ።ይህ የተጋነነ ማቃለል የመጣው ምናልባት ሮሜዋውያን ካቶሊኮች የተጋነነ ማክበር ስለሚያከብሯት ለዛ ተቃርኖ ከማሳየት አዝማሚያ ሊሆን ይችላል። ስለዚህም ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን አንዱንም የእርሷን በዓል አያከብሩም።  (2) አንዳንዶቹ የፕሮቴስታንት ወገኖች ድንግል ማርያምን “እህታችን” ይሏታል። (3) በተጨማሪ አንዳንዶቹ ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ጌታ ኢየሱስን በድንግልና ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር ጋብቻዋን ፈጽማለች፤ የ‘ኢየሱስ ወንድሞች’  ወይም የ’ጌታ ወንድሞች’ ተብለው የተጠሩ ልጆችን ወልዳለች ይላሉ።  (4) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ቤተክርስቲያናችን ለድንግል እመቤታችን የሰጠቻቸውን አንዳንድ የማዕረግ ስሞችም ይቃወማሉ።  (5) ድንግልን ያለማክበራቸው አንዱ...

ስለ "አስታዋሽ ጾምና በዐሉ" ጥያቄና መልስ

 ስለ "አስታዋሽ ጾምና በዐሉ" ጥያቄና መልስ  ለዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ፦ ሕልውናችንን-ነጻነትችንን የማረጋገጥና የማስቀጠል አንድነታችንን የመጠበቅና የማጠንከር  በእሴቶቻችን የመደሰት፣ እነርሱን የመንከባከብና የማስተዋወቅ  በረከታችንን የማብዛትና የማካፈል  ኃላፊነቶቻችንን በማኅበር ፣ በማስተዋልና በትጋት እንድንወጣ “ጾሙና በዐሉ" አስታዋሽ ባሕላዊ ምልክታችን ይሁንልን   ጥያቄ 1 ፡ አድማጭ ተመልካቾቻችን እንኳን ደህና መጣችሁ።የከበረ ሰላምታችን ይድረሳችሁ። ዛሬ የምንወያየው ከአቶ ባንቱ ገብረማርያም ጋር ይሆናል። አቶ ባንቱ በሙያው ፋርማሲት ነው። እንደነገረኝ በእምነቱ ደግሞ ባፕቲስት ነው።ለዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ ባሕላዊ ምልክት የሚሆን “ጾምና በዐልን” በማስተዋወቅ ላይ ይገኛል። የምንወያየውም ስለዚሁ "ጾሙና በዐሉ" ምልክትነት ይሆናል።  አቶ ባንቱ ለመወያየት  ወደ እኛ በመምጣትህ አመሰግንሃለሁ። እንኳን ደህና መጣህ። አንተ እያልኩ ልቀጥል ወይስ አንቱ? መልስ 1፡ ዎገኔ፡   እንኳን ደህና ቆየኸኝ። ለአድማጭ ተመልካቾቻችሁም ሰላምታዬ ይድረስልኝ። አንተ በለኝ። የሚያውቀኝ ሁሉ አንተ ነው የሚለኝ።  ጥያቄ 2 ፡ እሺ  አንተ እያልኩ እቀጥላለሁ። አቶ ባንቱ፣ ምናልባትም ብዙ ሰው ስለማያውቅህ  እስቲ ስለራስህ በአጭሩ ንገረን። ወዲያውም መክፈቻ ይሆነናል መልስ 2 ዎገኔ ፦ አስቀድሜ ይኸን ዕድል ስለሰጠኸኝ ላመሰግንህ እወዳለሁ። አድማጭ ተመልካቾችህንም ጊዜ ወስደው  ውይይቱን  ስለሚከታተሉ ላመሰግናቸው እወዳለሁ።አዎን፣ ባንቱ ገብረማርያም እባላለሁ።እንደነገሩኝ የተወለድኩት ሽርካ በዛሬ አጠራሩ በአርሲ ዞን ነው።ነፍስ ያወቅሁትና ትምህርት ...