ለፓስተር ግርማ ቤካ ይህ የመጀመሪያው ጽሑፌ በዩ ትዩብ ለማቅረብ እንዲስማማ የተደረገ ነው። አድማጭ ተመልካቾቼ እንደምን ሰነበታችሁ? እኔ ቸርነቱ የበዛ አምላክ ይመስገንና ደህና ነኝ። የዛሬ ዝግጅቴ አንድ ፓስተር ወንድሜ ለተናገረው ምላሸ የሚሰጥ ነው። የአርሲ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች የደረሰባቸውን ግፍ ከኦርቶዶክሳውያኑ ጎን በመሆን ያወገዙ የወንጌል አማኞች ነበሩ። ይኸንን የወንጌል አማኞች ድርጊት “አታሽቃብጡ” በማለት ይኸው ወንድማችን ተቃውሞታል።የተቃወባቸውን ስምንት ምክንያቶች ነጥብ በነጥብ እያነሳሁ የራሴን አጭር ምላሽ የምሰጥባቸው ይሆናል። ከአጭር ምላሹ በኋላም ማብራሪያን አስከትላለሁ። በመጨረሻም ሐሳቤን አጠቃልላለሁ።በስፋት ከተደመጠ ቀና ውይይት ይከፍታል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። በዚህ አጋጣሚ ቤተሰብ የተገደለባቸውን እግዚአብሔር አምላክ ያጽናናችሁ ለማለት እወዳለሁ። ያፈሩትን ሐብትና ንብረት በትነው፣ ለዘመናት ከኖሩበት ቀዬ እንዲሰደዱ ለተገደዱት ወገኖችም ስቃያችሁን እግዚአብሔር “ሕይወትን ለማዳን” ያድርግላችሁ እላቸዋለሁ። አሁን ወደ ምላሹ፡ የተወደድክ ፓስተር ወንድሜ: ለጤናህ እንደምን አለህ? እኔ ቸርነቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን ደህና ነኝ። በአርሲ ግፍ ለተቀበሉት ኦርቶዶክሳውያን ድምጽ ላሰሙቱ የወንጌል አማኞች “አታሽቃብጡ" በሚል ሐሳብ ዙሪያ የተናገርከውን በአንክሮ አዳምጬ ከጨረስኩ በኋላ ግልጽነትህንና ስሜትህን ለመግለጥ መድፈርህን አድንቄአለሁ።ይኸው ድፍረትህ እኔንም እንድናገር አነቃቅቶኛል። ወንጌላዊ አማኝ ብሆንም በአርሲ ኦርቶዶክሳውያን የደረሰውን ግፍ ካወገዙት ጋር ...