Skip to main content

ለፓስተር ግርማ ቤካ


ለፓስተር ግርማ ቤካ

አድማጭ ተመልካቾቼ እንደምን አላችሁ? እኔ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁንና ደህና ነኝ። ይህ  የአርሲ ኦርቶዶሳውያንን መገደል በተመለከተ  ለፓስተር ግርማ ቤካ የሚተላለፍ መልእክቴ ነው።  ከታች ልናገርባቸው ያሉትን ጉዳዮች በዩትዩብ ሲናገር የሰማሁት እርሱን ነውና።

ይሁን እንጂ ከግርማ ቤካ ሐሳቦች ብዙውን የሚጋሩ ፓስተሮች እንዳሉ እገምታለሁ።ስለዚህ መልዕክቴ ለአንድ ሰው የተላለፈ ቢሆንም፣ ተመሳሳይ ሐሳብ ላላቸውም የሚዛመት ነው። በሌላ በኩል ግን ሐሳቡን ጨርሶ የማይጋሩት የወንጌል አማኝ ፓስተሮች  እንዳሉም ከግርማ ቤካ ንግግር መረዳት ይቻላል።

 የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ጭፍጨፋ አሳሳቢ ነው። ጉዳዩን የሰብዐዊ መብት ተሟጋቾች እንዲይዙትና ክትትል እንዲያደርጉበት ተስፋ አደርጋለሁ። በዚህ አጋጣሚ  ቤተሰብ  የተገደለባቸውን እግዚአብሔር አምላክ ያጽናናችሁ፣ የአርሲ ሕዝብንም አይዟችሁ ፥ የአብርሃም አምላክ ያያችኋል ለማለት እወዳለሁ።

  ይህን ካልኩ በኋላ የፓስተር ግርማ ቤካን ሐሳብ ነጥብ በነጥብ  እያነሳሁ   በየነጥቡ ሥር የራሴን አጭር መልስ እሰጣለሁ፤ ማብራሪያዬንም አስከትላለሁ። አቀራረቡ እስከመጨረሻው እንደዚህ ይቀጥላል። በስፋት ከተደመጠ ቀና ውይይት ይከፍታል ብዬም አምናለሁ።

የተወደድክ ወንድሜ ፓስተር ግርማ ቤካ፡- ለጤናህ እንደምን አለህ? እኔ ቸርነቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን ደህና ነኝ።

"በአርሲ ለተገደሉት ድምጽ ላሰሙቱ አታሽቃብጡ" በሚል ሐሳብ ዙሪያ የተናገርከውን በአንክሮ  አዳምጬ  ከጨረስኩ በኋላ ግልጽነትህና ስሜትህን ለመግለጥ መድፈርህን አድንቄአለሁ።ይኸው ድፍረትህ እኔንም እንድናገር አደፋፍሮኛል። በመሆኑም በአክብሮት የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ግድያ ካወገዙት ጋር እንደምቆም ለመግለጥና ምክንያቴን ለማብራራት ተነሳሳሁ። በገሐድ ምላሽ መስጠቴም  መልዕክትህ ገሐድ ስለነበረ ነው። 

ስለአታሽቃብጡ

ግድያውን ለሚያወግዙት አታሽቃብጡ ማለት  የአርሲ ኦርቶዶክሳውያንን ሰብአዊ መብት መከበር አታግዙ የማለት ያህል ነው።  ለተበደሉና ለተጨነቁ  መተጋገዝ እስከዚህም መራር ሊያደርግ እይገባም።

ማብራሪያ፡ የማሽቃበጥን ትርጉም ከቃላት መፍቻ ተመለከትኩና  በተናገርከው አኳያ የሚገጥመውእወደድ ባይነትሆኖ አግኝቼዋለሁ።የጠላኸው ማሽቃበጥ ለኦርቶዶክሳውያኑ አብሮ መጮሁን እንጂ እንደ ባሕርይ የጠላኸው መሆኑን ንግግርህ አያመለክትም። ለማንኛውም ኦርቶዶክሶውያኑ ድምጻቸውን ባስተጋባላቸውም ለእኔ ያላቸው ሐሳብ እንደማይለወጥ የታወቀ ነው። መጀመሪያውኑም የሚቃወሙኝ  የእኛን መከራ/ሞት አላወገዝክም ብለው አልነበረምና። ይህን በማድረጌ የሚለውጡት ነገር አይኖርም። የሚቃወሙኝ "መንጋችን በጎቻችንን የምትወስድ ተኩላ ነህ" ብለው ነው። ስለዚህ እንደተቀበልኩት የሆነውን ወንጌል ማካፈሌ ስለማይቀር ሊወዱኝ አይችሉም።ልወደድ ብዬ የማደርገው አለመሆኑ ግልጽ ይመስለኛል። አላሽቃበትኩም።ምክንያቴን ለማወቅ ከጓጓህ

በሕንጸት መጽሔት "መከራው እስካለ" በሚለውና "አዎን ድምጽ" ድኅረ ገጽ "እግዚአብሔር የጠላቶቼ ጠላት አይደለም"! በሚለው ርዕስ ከጻፍኩት ማግኘት ትችላለህ። ለማንኛውም በገባኝ መጠን የዜጎች የመኖር መብትን ከሚያቀነቅኑ ጋር ለመተባበር እመርጣለሁ።

      “እንደ እኛ መከራን በፀጥታ ይቀበሉ” ስለሚለው

 ፍትሕ በጎደለበት ላይ ዝምታ ፦ጨቋኙን ከመርዳትና  በደልን ከማጽደቅ አንድ ነው።እውነት ነው፣  እንደ ክርስቲያን በመከራ መታገሥ ይገባል።ይህ ግን ፍትሕን ከመፈለግ  ጋር አይጋጭም። ስለዚህ ኦርቶዶክሳውያኑ ፍትሕን ይፈልጉበት፣ ጸጥ አይበሉ እላለሁ።

ላስረዳ፡ ክርስትያን የሚሰደድ መሆኑን ስለማወቅ ለኦርቶዶክሶች መንገር ለቀባሪው አረዱት ነው። የምንወቅስባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም ከነዚያ ዝርዝር ውስጥ ይህ አይገኝበትም።"ዘመነ ሰማዕታት" የተሰኘው የቀን አቆጣጠራቸው ይህ እንዳይዘነጋቸው የሚያስታውሳቸው  ነው። ምናልባት እኛም መጽሐፍ ቅዱስ ስላስተማረን ብቻ ሣይሆን በኅሊናችን ከዚያ ይዘን በመጣነውም ስሜትና ባሕልም ይመስለኛል መከራን ለመቀበል የተደፋፈርነው። ስለዚህ መከራን በትዕግሥት ስለመቀበል የምንጨምርላቸው ብዙ ዕውቀት ያለ አይመስለኝም። ይሁን እንጂ በመከራ መታገስ ማለት ፍትህን አይጠይቁ ማለት አይደለም።

    ከዚህኛው ነጥብ ጋር በተገናኘ ከተናገርከው ውስጥመከራ ለክርስቲያን ያለ ነገር ነውና እኛ ዝም ብለን እንደተቀበልነው ዝም ብለው ይቀበሉየሚለው ኅይለ ቃል ይገኝበታል። በዚህ  እኛን የሞራል መለኪያ አድርገሃል። ስለ መከራች ዝም እንዳላልን ግን የምታውቅ ይመስለኛል።በመከራችን ውስጥ እግዚአብሔር ስላሳለፈን ወይም ስለከለለን በምስክርነታችን፥ በመዝሙራችን አሁን አሁን በመጽሐፎቻችንም የምናነሳው ነው። "እንደ ሁለተኛ ዜጋ ስንታይ ኖረናልየሚለውን ወቀሳም አንተው አንስተኸዋል። እነዚህ ሁሉ ስለመከራችን ዝም ያልን አለመሆናችንን የሚያሳዩ ናቸው። አንጩህ እንጂ  እነዚህ ሁሉ ፍትህ እንፈልግ እንደነበር የሚያሳዩ ናቸው።ስለዚህ ትክክለኛ ማሳያ አልመረጥክም። በእርግጥ ስደትን አቁሙልን ብለን  ሰልፍ የወጣንበት ጊዜ አይታወስም። የቁጥር ኃይላችን (ብዛታችን) ውስን ነበረና። አንድ ላይ በሰልፍ ወጥተን "አታሳዱን" ብለን አልጮህንም። ለመጪው ዘመን ግን ሲያስፈልግ በሰልፍ ለመውጣት አሁን እየተሟሟቅን እንገኛለን። 

 “ሰርጎ ገብ ኦርቶዶክሶችን እንመነጥራለንያልከው ኅይለ ቃልም ይኸንኑ ግፊት የሚያመለክት ቀስት ነው።ስለዚህ ድምጻችን ጆሮ ያስገኝልናል ብለው ባሰቡት መንገድ አቤቱታቸውን ሲያሰሙ አታግዟቸው ዝም ይበማለት አፈናን ማበረታት ነው።  ከዚህ እርቀን ይልቁንም ድምጻቸውን እናስተጋባ።

 “አሳዳጆቻችን ነበሩ” ስለሚለው

ያለፈ በደል የዛሬውን ግድያ ላለመቃወም ሰበብ ለመሆን አይበቃም። ከቂም የተነሣ የግድየለሽነት አዝማሚያ ማሳየት ከአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ጨፍጫዎች ጋር  ማበር ሆኖ ይገኛል።  እንዲህ ዐይነቱ ሐሳብና ድርጊት ቢቀር እላለሁ።

 ላብራራው ኦርቶዶክሶች አሳደውናል ባልከው እስማማለሁ። የታሪክ እውነት ነው፣ አይካድም።ለብዙው ስደት የዐይን ምስክር  ባልሆንም ቢያንስ ስለአንዳንዶቹ ነበርኩ። ዝርዝሩን ልተወውና (አንተም አልገባህበትም) በደፈናው ባያሳድዱን ኖሮ መልካም ነበር እላለሁ። ድርጊቱን እነርሱ ምናልባትም ማሳደድ ብለው አይጠሩት ይሆናል።  ለማንኛውም የዚያ ቅያሜ /ቂም ትኩሱንና ገሐድ የሆነውን የአሁኑን የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ግድያን ከሚያወግዙት ጋር እንዳላብር ምክንያት ለመሆን አይበቃም። ታዲያ የ‍ኣሁኑ ሁኔታ ቢለወጥ  ኦርቶዶክሳውያን ያሳዱን ማለቴ  እንዳልሆነ ትረዳኛለህ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።ይልቁንም ባለፈው ጊዜ ማሳደዳቸው፣ ወንጌላውያኑን ከማደግ እንዳላገደን በመገምገም ተባብሮ የመሥራትን መንገድ ይመርጣሉ ፣ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። እኛም "እግዚአብሔር የጠላቶቼ ጠላት አለመሆኑን" ወደ መረዳት እናድጋለን የሚል እምነት አለኝ። 

      “ለእኛ ድምጽ ሆነው አያውቁም” ስለሚለው

ያለፈው አልፏል፣ ባለፈው አለመረዳታችን  ስለዛሬዎቹ ተገዳዮች ዝም ለማለት በቂ ምክንያት አይሆነንም። የመኖር መብታቸው ሲገፈፍ ከተጎዱት ጋር መቆም የሚገባን ፣  እነርሱ በፊት ከኛ ጋር ቆመው ስለነበር ወይም ሁኔታው ተስማሚ ስለሆነ አይደለም። ከተበደሉት ጋር መቆም ትክክል ስለሆነ እንጂ።

 ላፍታታው ለእኛ ድምጽ ሆነው አለማወቃቸው እውነት ነው። መከራ በደረሰብን ጊዜ ኦርቶዶክስውያን ስለ እኛ ተሟግተው የሚያውቁ አይመስለኝም።በበኩሌ  “ፕሮቴስታንቶችን አታሳዷቸው፣ መከራ አታምጡባቸውብለው ሲጮሁልን ሰምቼ አላውቅም። ብድር በምድር ይጽና ካላልክ በስተቀር በእኔ በኩል የብድራት ቀለበትን መስበር እመርጣለሁ። ለማንኛውም ዛሬና አሁን እልቂት እየደረሰበት ያለ የኦርቶዶክስ  ማህበረሰብ  አትግደሉኝ ብሎ ድምጹን ሲያሰማ ማገዝ ተገቢ ነው።አቅዶ ዝምታን መምረጥ እንዲያውም  ሌሎችንም አትተባበሯቸው ብሎ መምከር ግን የሰውን መብት ከሚጥሱ ጋር መተባበር ሆኖ ይታየኛል። 

      “መጥፋታችንን ይወዳሉ” ስለሚለው

ኦርቶዶክሳውያኑ እምነታችንን እንጂ የእኛን መጥፋት አይደለም የሚወዱት። የሰው ሕይወት  ከሃይማኖት ክርክር በላይ ነው። ልንተባበር የሚገባው በነገረ መለኮት መመሳሰል ላይ ተንተርሰን አይደለም።  ለተጎዱት ከሚጮኹ ጋር የምንተባበረው በሞራል ትክክል ስለሆነ ብቻ ነው።  

ልቀጥል፡ መጥፋታችንን ይወዳሉ የሚለው  ኅይለ ቃል ቢስተካከል  ስለኦርቶዶክሳውያን  የተናገርከው እውነት ነው።ያልተስተካከለው አባባል ኦርቶዶክሳውያኑ እንድንጠፋ የሚፈልጉት እኛን አለመሆኑ ነው።መስተካከል ያለበትም ይህ ነው። የእምነት ውድድር እንጂ በአካል የማጥፋት ፍላጎት አይደለም። ልክ እኛየኦንሊ ጂሰስእናየይሖዋ ምስክርትምህርት እንዲጠፋ ሰዎቹም ወደ እኛ እንዲመለሱ እንደምንፈልገው ማለት ነው።በአካል የመጠፋፋቱን መንገድ እኛም ፣ኦርቶዶክሳውያኑም የማናስበው ብልሆች ነን ለማለት እደፍራለሁ።ለጊዜው አልታይ ብሎን እንጂ በምሥራቅ አፍሪካ ዕጣችን አንድ ነው። የማድመጥ የገርነትና የመተባበር ዕድል በፊታችን አለ።ለማንኛውም ሕልም ፈርቼ ሳልተኛ ያደርኩበት ቀን የለምና ገና፥ ለገና ወደ ፊት ሊያጠፉኝ ይችላሉ ብዬ ከወዲሁ ይጥፋ ብዬ ዝም አልልም።የበቀል የቅድሚያ ክፍያ ከእኔ ይራቅ።  በሰላም በሚኖር ሕዝብ ላይ ግፍ ሲፈጸምበት መብቱ ሲጣስ ዝም ብሎ ለመመልከት ምክንያት አይሆነኝም።፡ የተገደሉት ስዎች መንግሥት ጥበቃ ሊያደርግላቸው የሚገባቸው ዜጎች ነበሩ። የሰው ሕይወት  ከሃይማኖት ክርክር በላይ ነው።  

  “ የግብጽና የኤርትራ አጀንዳ ተሸካሚዎች ቢሆኑሰ” ስለሚለው

 ስለ ጠላት አጀንዳ የሚኖር ክስ ለተበዳዮች ድምጽ መሆንን አይደፈጥጥም። የሰላማዊ ዜጎች ሕይወት ከፓለቲካ አጀንዳ በላይ ስለሆነ በዚህ ሰበብ ትብብርን መንፈግ ትክክል አይደለም። ካስፈለገ ፖለቲካውን በሌላ መንገድ መከታተል ይቻላል።

ዝርዝሩን ላቅርብ ፡ የግብጽና የኤርትራ አጀንዳ ተሸካሚ መሆን አለመሆናቸውን ሙሉ ሰው ስለሆኑ ራሳቸው ኦርቶዶከ‍ሳውያኑ ይናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትርም ቢሆኑ የኢምሬትን ፈቃድ፥ምክርና ሁለንተናዊ ድጋፍ ተከትለው ነው የሚሠሩት ይባላል። እርሳቸውም ይህን  ሲያስተባብሉ አልሰማሁም፡፡ የምታውቀው ካለ ስለዚህም የተጣራውን ወሬ ብትነግረን የተሟላውን ሥዕል ለማየት ይረዳናል።

   ለማንኛውም መልስ እንድሰጥበት የሚመለከተኝየኤርትራና የግብጽ አጀንዳ ተሸካሚ ሊሆኑ ስለሚችሉ አትጩህላቸውየሚለው ሐሳብ ስለሆነ ይህ ክስ  የመኖር መብታቸዉን በግፍ ለተቀሙት ድምፅ ሲሆኗቸው እንዳልተባበራቸው ለምክንያትነት አይበቃም እላለሁ። የሰው ሕይወትን እና ሰብአዊ ክብርን የላቀ ዋጋ መስጠት ተገቢ ነው።

የአሰብ ወደብ ጉዳይን ላንሳ

    ብቻ  ስለኤርትራና ግብጽ ያነሳኸው የአሰብን ወደብ  ከማስመለስ ጋር አያይዘህ ሳይሆን አይቀርም። እነዚህ አገሮች  የሚነሱት ከዚያ ጋር ተያይዞ ነውና። የወደቡ ነገር  ከተነሣ አይቀር  እኔም ጎራ ልበልበት።ኢትዮጵያ ወደብ ያስፈልጋታል። ነገር ግንከወደቡ በፊት ከኤርትራ ሕዝብ ጋር ስለመቀራረብ/ አንድ ስለመሆን መነጋገሩ አይሻልም?” እላለሁ። ከኤርትራ ጋር የሚያስማማ ነገር ቢኖር ይመረጣል ባይ ነኝ። በጦርነት ማስመለስ ይሻላል ብለው ካደረጉት ውሣኔው የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ነው። በብሔር በተሸነሸነች ኢትዮጵያ ወደቡ ሲመለስ ከሚገኘው በረከት ይልቅ የሚከተለው ሻሞና ከተመለሰ በኋላ በእጅ አቆይቶ ለመገልገል የሚፈጀው ማገዶ የሚያሳስበኝ መሆኑን ግን መሸሸግ አይቻለኝም።

    በእርግጥ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩበታሪክ አሰብን ያስመለሱ ጀግናለመባል ልባቸው ሳይመኝ ስለማይቀር በባሌም ሆነ በቦሌ  ይሞክሩት ይሆናል።ከተነሣ አይቀር ይህ እንደ አንድ የሚያስብ ዜጋ በእግረ መንገድ ያቀረብኩት የግል አስተያየቴ እንጂ የፖሊሲ ምክር አይደለም። ሙያዬ አይደለም። ከተነሳሁበትም ጉዳይ ጋር ቀጥተኛ ግኑኝነት የለውም። ለማንኛውም ክሱ ጋር አያይዘህ  ለኦርቶዶክሳውያኑ ከሚጮሁ ጋር አትጩሁ ላልከው ከላይ መልስ ሰጥቼአለሁ።

  “የብልጽግናን  መንግሥት ይጠላሉ” ስለሚለው

 መንግሥት የዜጎችን የመኖር ዋስትና  ማረጋገጥ ሕጋዊ ግዴታ አለብትየተፈጸመውን ግድያ  እውቅና መስጠትና በደሉን  መመርመርም ኃላፊነቱ ነው።።ሥራውን ሳይሠራ ሲቀር በኃላፊነት ጠየቅ  እርሱን መጥላት አይደለም።

የአያያዝካቸውን ላንሳ፡ ከዚህኛው መንግሥት በፊት የነበሩትን ሳይቃወሙ ይህንን መንግሥት ብቻ ተቃውመዋል በማለት በአርሲ ስለ ተገደሉት ኦርቶዶክሳውያን የጮሁትን  ለአሁኑ መንግሥት ጥላቻ ስላላቸው ነው የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰሃል።

    ምናልባት ፓለቲካና ኮረንቲ በሩቁ እንል ከነበርነው መኻል ሆነህ ይሆናል እንጂ የቀደሙትንም መንግሥታት የሚቃወሙ ኦርቶዶክሳውያን ነበሩ።የአሁኑን መንግሥት ስለመቃወማቸው በቂ ምክንያት የላቸውም ካልክ ሞግታቸው።የሠራውን መልካም ሥራ ለማጨናገፍ ነው ካልከም ተከራከራቸው። በበኩሌ መገደላችንን ያስቁምልን ብለው  በመጮኻቸው መንግሥትን ነክተዋል ብዬ በመቀየም የአርሲ ኦርቶዶክሳውያንን መገደል ከማውገዝ  አልመለስም::

     ከዚሁ ጋር አያይዘህ (ባለፈው ግዜ በነነዌ ጾም ሞዴልነት መጾማቸውንና ጥቁር  መልበሳቸውን መሆኑ ነው መሰለኝ) በመንግሥት ላይ የአመጽ ቅስቀሳ አድርጋችኋል ብለሃቸዋል። ጾም ማወጃቸውና ጥቁር መልበሳቸውን ግን እንደ እምነታቸው ስለአገሪቷ ንስሐ መግባታቸውና መከራው እንዲቀር መጸለያቸው ነበር እንጂ አንተ እንዳስመሰልከው በመንግሥት ላይ የአመጽ ጥሪ አልነበረም።በንስሐ ሥርዐቱ ላንስማማ እንችላለን።  የሥርዐቱን ዐላማ ማዛባት ግን አይገባም።

     እርግጥ እንዲያ እንዲሆን የሚፈልጉ የመንግሥት ተቃዋሚዎች አልነበሩም ብዬ መናገር አልችልም።ከእነዚያ ወገኖች አንዳንዶቹ "ያኔ አመጽ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ  ቤተክርስቲያን እስከ አሁን ከችግሯ ትላቀቅ ነበር" ብለው በቁጭት የሚናገሩ ሰምቼአለሁ። ከጥቁር መልበሱ ጋር ሌሎች የማወኪያ ዘዴዎችን የዘረዘርካቸውም የሽርደዳ ንግግር እንጂ እውነትነት ያላቸው አይመስሉም።ግራም ነፈሰ ቀኝ "በመንግሥትን ይጠላሉ ሰበብ" ግድያውን ማውገዝ ሊከለከሉ አይገባም።እኛም ከመተባበር።

የኦሮሞን ስም  ያጠለሻሉ” ስለሚለው

ግፍ የፈጸሙት ግለሰቦች ናቸው፤ የኦሮሞ ሕዝብ አይደለም።የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ግድያ የኦሮሞ ሕዝብ ስም  ከማጠልሸትም ከመሸላለምም ጋር ግንኙነት የለውም። ከማጠልሸት ጋር ማገናኘቱ ጭፍጨፋው  እውቅና እንዳያገኝና ግፍ እንዳይጋለጥ አቅጣጫ ማስቀየስ ሆኖ የሚታይ ነው ።

ስለተያያዘው ርብርብ ልግለጥ፡ መንግሥትን ከመጠየቅ ይልቅ ጉዳዩን ሕዝብን ወደማነካካት አዞርከው። የኢትዮጵያ መሪዎቹ የወጡበትን የከበረውን የኦሮሞ ሕዝብ ስሙን ያጠለሻሉ በማለት አደገኛ ነገር አደረግህ። አርሲን የምታውቀው ከሆነ በዚያ ያሉ ኦርቶዶክሳውያን አማራ ተብለው ስለሚጠሩና (እስከማውቀው ድረስገዳዮቹም አማራን ገደልን ሰለሚሉ ኦሮሞ ተወቃሽ እንደተረገ መስሎህ ይሆናል።

በእርግጥ ኦርቶዶክሳውያኑ አማራ ተብለው እስከተጠሩ የሚገደሉትም  አማራ ተብለው እስከሆነ ድረስ ከአማራ ተጋዳዮች ጋር እንዲሰለፋ የሚቀሰቅሱ አሉ። እነዚያ ኃይሎች አማራ በሃይማኖት በመኖሪያ አካባቢና በመሳሰለው ውስጥ የመጋደል አቅሙን ከሚበታትን፣ ኃይሉን በአንድ ላይ በአንድ አማራነት ከረጢት ቢያስቀምጥ ተቃውሞው ውጤታማ ይሆናል ብለው ይወተውታሉ። 

መንግሥትም በበኩሉ እጁን አጣጥፎ አልተቀመጠም።አብረውት ከሚሠሩ ጋር በመሆን ይህ እንዳይሆን አስከሬን ቆጠራውን በዘር እየሽነሸነ ያቀርባል የሌሎች ሃይማኖት ሰዎችም ተገድለዋል በማለት ጥያቄውን ለማፋዘዝ ይተጋል። "ግድያው ከሃይማኖት ጋር ግንኙነት የለውም ብሎም ነገርን ለማስቀየስ ይሞክራል።ታዲያ በዚህ መኻል ከፍትህ ጠያቂዎቹ ኦርቶዶክሳውያን የኦሮሞን ማሕበረሰብ የሚወቅስ ምን ንግግር ሲያደርጉ ተሰማህየኦሮሞ ማኀበረሰብን የሚነካ ነገር የለበትም። ሊነካም አይገባም።

    ባይሆን ጉዳዩ የተፈጸመው በኦሮምያ ክልል ስለሆነ የኦሮሚያ ስሙ ጠፋ የሚለው ወቀሳ ያስኬዳል። ለዚህ መድኅኒቱ "በጎ ነገር ሲደረግ  ኦሮምያ ክልል፥ "ክፋ ሲደረግ ግን  ክልል 4" እያሉ መናገር ይሻል ይሆን? እላለሁ። 

ለማንኛውም በአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰባቸው ግድያ መሠረታዊ የመኖር መብትንና የሰውነት ክብርን የሚዳፈር ጉዳይ ስለሆነ በሕዝብ ውስጥ መሸሸግ አይቻልም። ጉዳዩን አጣርቶ ወንጀለኞችን ለሕግ ማቅረብ  የመንግሥት ኃላፊነት ነው።

          “ሰርጎ ገብ ኦርቶዶክሶችን እንመነጥራቸዋለን” ስለሚለው

ይህ ጫፍ ረገጥና አደገኛ ንግግር ነው። ደግነቱ  የክርስቶስ ሃሳብ ስለሚገባህ  ለመታረም የሚከብድህ አይመስለኝም።።

 የተደነቅሁበትን ላክል የኦርቶዶክሶች  ወንጌል አማኞች  ዘንድ ሠርገው መግባታቸውን አላውቅም ነበር። ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት ከአንተ ነው። እኛ እነሱጋ ሰርገን ገብተናል ሲባል ሰምቼ አውቃለሁ። እንዳውም በእቅድ ይህንን የሚያደርጉ እንዳሉ ተረድቼአለሁ።  ምክንያታቸውም ነፍሳትን ለማዳን ነው። የኦርቶዶካሳውያን  እኛጋ ሰርጎ መግባት ግን እንግዳ  ነገር ሆኖብኛል። አስደንቆኛል። እውነት  ከሆነም እንደ ሰው ስገመግመውሰርጎ ገብ ኦርቶዶክሳውያንን እንመነጥራለን" የሚለው ቃል አስጨናቂ ነው።ወንድሜ ግርማ እንዲህ ዐይነቱ ክፋ ሐሳብ ካንተ ይራቅ። መቼም ከክፋት ለመራቅ  የልብ ትህትና እና ቅንነት እንዳለህ ባምን ጀዝባ የምባል አይመስለኝም።

እንደዚህ ልቋጨው

    ምንም እንኳ  የአርሲ ኦርቶክሳውያን መገደል ከሃይማኖትና ከዘር ያለፈ ጉዳይ ቢሆንም ኦርቶዶክሳውያኑ ግምባር ቀደም አውጋዥ   በመሆናቸው የአለመተባበር ሃሳብህንና ሌሎቻችንም እንዳንተባበር መፈለግን እንደምታነሳ ይታየኛል። 

ምክንያቱም የኦርቶዶክሳውያን  ስለበጎቻቸው የሚያሰሙትን አቤቱታ እንደ ፓስተር ሆነህ በማሰብ  ርኅራኄን እንደምታሳያቸው ተስፋ ስለማደርግ ነው።ደግሞም በቪዲዮ እንዳየሁህ አዲስ ነገር ለመማር የሚችል ዕድሜ ላይ ያለህ ስለሚመስል ፈጥነህ ይኽን ትገነዘባለህ ብዬ አምናለሁ።

 እኔ ግን "ኦርቶዶክሳውያን አትግደሉን ማለታቸውን አታስተጋቡ /አታሽቃብጡ" ያልከውን ምክር ወይም ተግሣጽ ለመቀበል ከላይ እንዳተትኩት ምክንያቶቹ  ሁሉ በቂ  ሆነው አላገኘኋቸውምና እምቢታዬን  በታላቅ ትህትና እንድገልጽ ፍቀድልኝ። 

በመጨረሻም  የምንሰጠው አስተያየትና የምንይዘው አቋም ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ካላቸው የሞራል መርሖች ጋር የሚስማማ ሊሆን ቢችል እላለሁ። "በሰሜንም በደቡብም ላለው አድልዎ ሳናደርግ ዘርና ሃይማኖት ሳንመርጥ ለሰው በሰውነቱ ብቻ እንጮህለታለን" ብለህ የተናገርከውን  ድንቅ ነገር በአርሲ ለተገደሉት ኦርቶዶክሳውያንም እንዳፍህ ያድርገው እላለሁ።በአርሲ ርኅራኄ፣ ፍትሕና ተጠያቂነት እንዲሰፍን ተስፋ በማድረግ  ልሰናበትህ።

ስለአዳመጥከኝ አመሰግንሃለሁ። አድማጭ ተመልካቾቼንም  በትዕግሥት ስለተከታተላችሁኝ አመሰግናለሁ። 

ደህና ሰንብቱልኝ።

ባንቱ ገብረማርያም

ከአዎን ድምፅ

 

Comments

Popular posts from this blog

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ (1)  ድንግል ማርያምን ስለማክበር (2) ለጥያቄዎች መልስ (ሀ) ድንግሊትን ‘የወይን ግንድ (ተክል)’ና የ ‘ሕይወት በር’ የሚል ማዕረግ  ለምን እንሰጣታለን? (ለ) ወደ ድንግል ማርያም መጸለይ ትክክል ነው ወይ? (3) የድንግል ማርያም ድንግልና ዘላለማዊነት (4) ለተቃራኒ አስተያየቶች መልስ (ሀ) “የመጀመሪያ ልጇን” የሚለው ሐረግ (ለ) “ሚስትህ” የሚለው ሐረግ (ሐ) “አብረው ከመሆናቸው በፊት ጸንሳ ተገኘች” (መ) “የመጀመሪያ ልጇን እስክትወልድ አላወቃትም” (ሠ)  “ወንድሞቹ” የሚለው ሐረግ   የቅድስት ድንግል ማርያም  ክብሯ (1) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ድንግል እመቤታችንን አያከብሩም፤ ደግሞም እንድታማልድላቸውም (እንድትማልድላቸውም)  አይጠይቋትም።ከእነርሱ ወገኖች አንዳንዶቹ እንዲያውም ጫጩቱ ከተፈለፈለ በኋላ ዋጋ ከሌለው የዶሮ እንቁላል ቅርፊት ጋር እስከሚያመሳስሏት ይደርሳሉ።ይህ የተጋነነ ማቃለል የመጣው ምናልባት ሮሜዋውያን ካቶሊኮች የተጋነነ ማክበር ስለሚያከብሯት ለዛ ተቃርኖ ከማሳየት አዝማሚያ ሊሆን ይችላል። ስለዚህም ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን አንዱንም የእርሷን በዓል አያከብሩም።  (2) አንዳንዶቹ የፕሮቴስታንት ወገኖች ድንግል ማርያምን “እህታችን” ይሏታል። (3) በተጨማሪ አንዳንዶቹ ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ጌታ ኢየሱስን በድንግልና ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር ጋብቻዋን ፈጽማለች፤ የ‘ኢየሱስ ወንድሞች’  ወይም የ’ጌታ ወንድሞች’ ተብለው የተጠሩ ልጆችን ወልዳለች ይላሉ።  (4) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ቤተክርስቲያናችን ለድንግል እመቤታችን የሰጠቻቸውን አንዳንድ የማዕረግ ስሞችም ይቃወማሉ።  (5) ድንግልን ያለማክበራቸው አንዱ...

Comparative Theology የነገረ መለኮት ንጽጽር (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት)/ በብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ሲኖዳ ሳልሳዊ

 የነገረ መለኮት ንጽጽር  (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት): የወደደ  ሁሉ በነጻ እንዲጠቀምበት ተፖስቷል። ይሁን እንጂ መብቱ በሕግ የተጠበቀ ስለሆነ በየትኛውም መልኩ ለንግድ እንዲውል አልተፈቀድም። ልዩ ልዩ መግቢያ የሚለውን መጀመሪያ ካነበቡ በኋላ የተቀረውን በተመረጠው ቅደም ተከተል ማንበብ ይቻላል። ልዩ ልዩ መግቢያ   ጥምቀት   ትውፊት (ወግና ልማድ)   መካከለኝነት   ጾም የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ መንፈሳዊ ስጦታዎችና በልሳኖች የመናገር ስጦታ   ሥርዐት ንስሐ

ጥምቀት

  ጥምቀት       (1) የጥምቀት ፍቱንነቱ (2) ማጥመቅ የካህን ተግባር ነው (3) የጥምቀት አስፈላጊነቱ (4) ጥምቀት በመንከር (በመጥለቅ) (5) የልጆች (የሕጻናት) ጥምቀትሳቦች (6) ተቃውሞዎች   ጥምቀት   በእኛ በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንቶች መኻል ጥምቀትን በተመለከተ ያሉት ልዩነቶች የጥምቀትን ትምህርት በአምስት ጉልህ   ፍሬ ነገሮች ሥር አጠቃሎ መነጋገር ይቻላል። (1)     የጥምቀት   አስፈላጊነቱ   ምንድነው? ፍቱንነቶቹስ (ጠቀሜታዎቹስ) ምንድናቸው? ኦርቶዶክስ ጥምቀት ‘ድኅነት’ን፣ ‘መንጻት’ን፣ ‘መጽደቅ’ን፣ የ‘ሕይወት መታደስ’ን እና በ’ክርስቶስ አካል አባል’ መሆን’ን መቀበያ መንገድ ነው ብላ ታምናለች። የፕሮቴስታንት ቤተ እምነቶች እንደሚሉት እነዚህን   መቀበያው “እምነት” ብቻ ነው። በ እምነት ብቻ መሆኑ ትክክል ከሆነ ታዲያ የጥምቀት አስፈላጊነቱ ምኑ ላይ ነው? የክርስትና ምልክት ብቻ መሆኑ ነውን? ወይስ “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴ 28:19-20) የሚለውን የጌታን ትዕዛዝ መታዘዝ ብቻ መሆኑ ነው? (2 ) ማነው ማጥመቅ ያለበት? በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጥምቀት የሚከናወነው በካህን ብቻ ነው። ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ግን የሰውን ክህነት ጨርሶ አይቀበሉም። ስለሆነም በእነርሱ ቤተ ክርስቲያን የሚያጠምቀው ካህን ወይም ቄስ ያልሆነ አገልጋይ ነው።   ይህ አገልጋይ የቤተክርስቲያኒቷ ሽማግሌ ወይም ሴት ሽማግሌ (የሴቶችን ሽምግልና ...