የምታገኙት ለወንድሜ ፓስተር ግርማ ቤካ አድርሱልኝ!
ለፓስተር
ግርማ ቤካ
በአድራሻህ
ጉዳዩ፡-
ወንጌላውያንን ለኦርቶዶክሳውያን አታሽቃብጡ ስላልከው፡
የተወደድክ
ወንድሜ ፓስተር ግርማ ቤካ፡- ለጤናህ እንደምን አለህ? እኔ ቸርነቱ የማያልቅበት መድኅኒዓለም ይክበር ይመስገን ደህና ነኝ።
ለኦርቶዶክሶች
ከሚጮኹት ጋር አትተባበሩ/አታሽቃብጡ ያልከው መልዕክት ደርሶኛል።አባል የሆንኩባትን ቤተክርስቲያንም ሆነ ወንጌላውያንን ወክዬ ለመናገር መብት እንደሌለኝ ታውቃለህ። ነገር ግን ከወንጌላውያን መኻል እንደመቆጠሬ መጠን የግሌን አቋም ለመግለጥና ለማብራራት ነው ይህንን ደብዳቤ የምልክልህ። ይፋዊ ማድረጌም መልዕክትህ ይፋዊ ስለሆነ ነው።
ከሁሉ
አስቀድሜ ግልጽነትህንና ስሜትህን ለመግለጥ መድፈርህን ማድነቄን ልገልጽልህ እወዳለሁ። በመቀጠል ወደ ጉዳዩ ልግባና መጀመሪያ በዝርዝር የተናገርከውን በአጭሩ ሳስቀምጠው፡፡ በቀጥታ ምክንያት አድርገህ ባታቀርባቸውም ከቋንቋ አገባቡ እንደተረዳሁት ከኦርቶዶክሶቹ ጋር እንዳንተባበር (ማለትም እንዳናሽቃብጥላቸው) የሚከተሉትን በምክንያትነት ተናግረሃል።
1.
እንደ እኛ
መከራን በፀጥታ ይቀበሉ
2.
አሳዳጆቻችን ነበሩ
3.
ለእኛ ድምጽ
ሆነው አያውቁም
4.
መጥፋታችንን ይወዳሉ
5. የግብጽና የኤርትራ አጀንዳ ተሸካሚዎች ሊሆኑ ይችላሉ
6.
የአሁኑን ሸጋ መንግሥት ይጠላሉ
ከምክንያትነት
ውጭ በተጨማሪ የተናገርካቸው
7.
በሰሜንም በደቡብም
ላለው አድልዎ ሳናደርግ እንቆረቆራለን
8.
ሰርጎ ገብ
ኦርቶዶክሶችን እንመነጥራቸዋለን የሚሉ ናቸው
የዘነጋሁት ወይም ያዛባሁት ነገር ካለ እታረማለሁ።
በዚህ መረዳቴ መሠረት የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ግድያ መቃወምን በተመለከተ ከኦርቶዶክሳውያን ጋር አትባበሩ ያልከውን ምክርህንና ተግሣጽህን ያልተቀበልኩ መሆኔን እንዲሁም ለምን እንዳልተቀበልኩ አስረዳለሁ።በመጨረሻም መደምደሚያዬን እሰጣለሁ።
የማሽቃበጥን
ትርጉም ከቃላት መፍቻ ተመለከትኩና በተናገርከው አኳያ የሚገጥመው “እወደድ ባይነት” ሆኖ አግኝቼዋለሁ።የጠላኸው ማሽቃበጥ ለኦርቶዶክሳውያኑ መሆኑን እንጂ እንደ ባሕርይ የጠላኸው መሆኑን ንግግርህ አያመለክትም። ለማንኛውም ኦርቶዶክሶቹ ድምጻቸውን ባስተጋባላቸውም እንደማይወዱኝ የታወቀ ነው። መጀመሪያውኑም የሚቃወሙኝ የእኛን መከራ/ሞት አላወገዝክም ብለው አልነበረምና። ይህን በማድረጌ የሚለውጡት ነገር አይኖርም። የጠቡ መነሻ ከ"መንጋችን በጎቻችንን የምትወስድ ተኩላ ነህ" ብለው ነው። ስለዚህ እንደተቀበልኩት የሆነውን ወንጌል ማካፈሌ ስለማይቀር ሊወዱኝ አይችሉም።ልወደድ ብዬ የማደርገው አለመሆኑ ግልጽ ይመስለኛል። አላሽቃበትኩም።ምክንያቴን ለማወቅ ከጓጓህ የሚከተሉትን ሊንክ ከፍተህ እንድታነብ በታላቅ ትህትና እጋብዝሃለሁ።
You searched for መከራው እስካለ - Hintset
1. እንደ እኛ መከራን በፀጥታ ይቀበሉ
ክርስትያን የሚሰደድ መሆኑን ስለማወቅ ለኦርቶዶክሶች መንገር ለቀባሪው አረዱት ነው። የምንወቅስባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም ከነዚያ ዝርዝር ውስጥ ይህ አይገኝበትም።"ዘመነ ሰማዕታት" የተሰኘው የቀን አቆጣጠራቸው ይህ እንዳይዘነጋቸው የሚያስታውሳቸው ነው። ምናልባት እኛም መጽሐፍ ቅዱስ ስላስተማረን ብቻ ሣይሆን በኅሊናችን ከዚያ ይዘን በመጣነውም ስሜት/ባሕልም ይመስለኛል መከራን ለመቀበል የተደፋፈርነው። ስለዚህ ስለ ስደት የምንጨምርላቸው ብዙ ዕውቀት ያለ አይመስለኝም።
ከዚህኛው ነጥብ ጋር በተገናኘ ከተናገርከው ውስጥ “መከራ ለክርስቲያን ያለ ነገር ነውና እኛ ዝም ብለን እንደተቀበልነው ዝም ብለው ይቀበሉ” የሚለው ኅይለ ቃል ይገኝበታል። ነገሩ ለመንግሥት ሃዘኔታ ይመስላል።ይሁን እንጅ በዚህ እኛን የሞራል መለኪያ አድርገሃል። ስለ ስደታችን ዝም እንዳላልን ግን የምታውቅ ይመስለኛል።በመከራችን ውስጥ እግዚአብሔር ስላሳለፈን ወይም ስለከለለን በምስክርነታችን፥ በመዝሙራችን ፥ አሁን አሁን
በመጽሐፎቻችንም የምናነሳው ነው። "እንደ ሁለተኛ ዜጋ ስንታይ ኖረናል" የሚለውን ወቀሳ ማንሳትህም ይህንኑ የሚያሳይ ነው።ስለዚህ ትክክለኛ ማሳያ አልመረጥክም። በእርግጥ ስደትን አቁሙልን ብለን ሰልፍ የወጣንበት ጊዜ አይታወስም። የቁጥር ኃይላችን (ብዛታችን) ውስን ነበር። አንድ ላይ በሰልፍ ሊያስወጣን የሚችል ጉዳይም አልነበረንም። ለመጪው ዘመን ግን አሁን እየተጠረብን፥ እየተሞረድንና እየተሟሟቅን እንገኛለን። ሰርጎ ገብ ኦርቶዶክሶችን እንመነጥራለን ያልከው ኅይለ ቃልም ይኸንኑ የሚያመለክት ቀስት ነው።ስለዚህ ድምጻችን ሊሰማ ይችላል ብለው ባሰቡት መንገድ አቤቱታቸውን ቢያሰሙ አቤቱታቸውን ላለማስተጋባት ምክንያት አይሆነኝም። ርኅራኄ ለተጎዳ ይቀድማል።
2. አሳዳጆቻችን ነበሩ
ኦርቶዶክሶች አሳደውናል ባልከው እስማማለሁ። የታሪክ እውነት ነው፣ አይካድም።ለብዙው ስደት የዐይን ምስክር ባልሆንም ቢያንስ ለአንዳንዶቹ ነበርኩ። ዝርዝሩን ልተወውና (አንተም አልገባህበትም) በደፈናው ባያሳድዱን ኖሮ መልካም ነበር እላለሁ። ድርጊቱን እነርሱ ምናልባት ማሳደድ ብለው አይጠሩት ይሆናል። ለማንኛውም የዚያ ቅያሜ ትኩሱንና ገሐድ የሆነውን የአሁኑን የአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ግድያን እንዳላወግዝ ምክንያት ለመሆን አይበቃም።ይህን ስል የኣሁኑ ሁኔታ ቢለወጥ ኦርቶዶክሳውያን ያሳዱን ማለቴ እንዳልሆነ ትረዳኛለህ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።ይልቁንም ያለፈው ስደት ወንጌላውያኑን ከማደግ እንዳላገደን በመገምገም ተባብሮ የመሥራትን መንገድ ይመርጣሉ ብዬ አስባለሁ። እኛም "እግዚአብሔር የጠላቶቼ ጠላት አለመሆኑን" ወደ መረዳት እናድጋለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።
3. ለእኛ ድምጽ ሆነው አያውቁም
ይህም እውነት ነው።መከራ በደረሰብን ጊዜ ስለ እኛ ተሟግተው የሚያውቁ አይመስለኝም።በበኩሌ ሲናገሩ ሰምቼ አላውቅም።እንድገምት ቢፈቀድልኝ፡-ምናልባትም መከራ ሲደርስብን “ጎሽ፥ የታባታቸው፥ እንኳን ቀመሷት” ይሉም ይሆናል። ብድር በምድር ይሁን ካላልክ በስተቀር በእኔ በኩል የብድራት ቀለበትን መስበር እመርጣለሁ።
4. መጥፋታችንን ይወዳሉ
አባባሉ
ቢስተካከል ይህም እውነት ነው።ያልተስተካከለው አባባል “ጓድ” መንግሥቱ ኃይለማርያም በአንደኛው ዲስኩራቸው ፡-”ጥያቄው እነርሱ ይጥፉ ወይስ እኛ” ያሉትን አስታወሰኝ። እርሳቸው ዛሬ ዝምቧቤ ናቸው። ወደ እኛው ጉዳይ ልመለስና ፡- ኦርቶዶክሶቹ እንድንጠፋ የሚፈልጉት እኛን አይመስለኝም። መስተካከል ያለበትም ይህ ነው።እምነታችንን ይመስለኛል።ልክ እኛ “የኦንሊ ጂሰስ” እና “የይሖዋ ምስክር” ትምህርት እንዲጠፋ ፥ ሰዎቹም ወደ እኛ እንዲመለሱ (ልቀሽረውና ፥ ወደ እውነተኛው የመጽሑፍ ቅዱስ ትምህርት እንዲመለሱ) እንደምንፈልገው ማለት ነው።በአካል የመጠፋፋቱን መንገድ እኛም ኦርቶዶክሳውያኑም የማንመርጥ ብልሆች ነን ለማለት እደፍራለሁ።ለጊዜው አልታይ ብሎን እንጂ በምሥራቅ አፍሪካ ዕጣችን አንድ ነውና። የማድመጥ ፣ የገርነትና የመተባበር ዕድል በፊታችን አለ።ለማንኛውም ሕልም ፈርቼ ሳልተኛ ያደርኩበት ቀን የለምና ገና፥ ለገና ወደ ፊት ሊያጠፉኝ ይችላሉ ብዬ ከወዲሁ ይጥፋ አልልም።የበቀል የቅድሚያ ክፍያ ከእኔ ይራቅ።
5. የግብጽና የኤርትራ አጀንዳ ተሸካሚዎች ሊሆኑ ስለሚችሉ
ተሸካሚ መሆን
አለመሆናቸውን ሙሉ ሰው ስለሆኑ ራሳቸው ይናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትርም ቢሆኑ የኢምሬትን ፈቃድ፥ምክርና ድጋፍ ተከትለው ነው የሚሠሩት ይባላል። እርሳቸውም ሲያስተባብሉ አልሰማሁም፡፡ የምታውቀው ካለ ስለዚህም የተጣራውን ወሬ ብትነግረን የተሟላውን ሥዕል ለማየት ይረዳናል።
ለማንኛውም
መልስ እንድሰጥበት የሚመለከተኝ “የኤርትራና የግብጽ አጀንዳ ተሸካሚ ሊሆኑ ስለሚችሉ አትጩህላቸው” የሚለው ሐሳብ ስለሆነ ወደዚያ ልመለስ። በዚህ እርግጠኛ ባልሆንክበት ወሬ በአርሲ ለተገደሉት ድምጽ ማሰማታችንን ማስቀረት አለብን ማለት ነው? ከሆነ ይህን “በይታሰባል በቀል” እለዋለሁ። ገሐዱን ሰህተት እያዩ ማለፍ አግባብ አይደለም። ያደርሰናል! ተሸካሚ መሆናቸው እርግጥ የሆነ ጊዜ ልንቃወማቸው እንችላለን።
ብቻ
ስለኤርትራና ግብጽ ያነሳኸው የአሰብን ወደብ ከማስመለስ ጋር አያይዘህ ሳይሆን አይቀርም።የወደቡ ነገር ከተነሣ አይቀር እኔም ጎራ ልበልበት።ኢትዮጵያ ወደብ ያስፈልጋታል። ነገር ግን “ከወደቡ በፊት ከኤርትራ ሕዝብ ጋር ስለመቀራረብ/ አንድ ስለመሆን መነጋገሩ አይሻልም?” እላለሁ።ከኤርትራ ጋር የሚያስማማ ነገር ቢኖር ይመረጣል ባይ ነኝ። በጦርነት ማስመለስ ይሻላል ብለው ካደረጉት ውሣኔው የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ነው። በብሔር በተሸነሸነች ኢትዮጵያ ወደቡ ሲመለስ ከሚገኘው በረከት ይልቅ የሚከተለው ሻሞና ፥ ከተመለሰ በኋላ በእጅ አቆይቶ ለመገልገል የሚፈጀው ማገዶ የሚያሳስበኝ መሆኑን ግን መሸሸግ አይቻለኝም ።
በእርግጥ
ክቡር ጠቅላይሚኒስትሩ “በታሪክ አሰብን ያስመለሱ ጀግና” ለመባል ልባቸው ሳይመኝ ስለማይቀር በባሌም ሆነ በቦሌ ይሞክሩት ይሆናል።ከተነሣ አይቀር ይህ እንደ አንድ የሚያስብ ዜጋ በእግረ መንገድ ያቀረብኩት የግል አስተያየቴ እንጂ የፖሊሲ ምክር አይደለም። ሙያዬ አይደለም። ከተነሳሁበትም ጉዳይ ጋር ቀጥተኛ ግኑኝነት የለውም\
6. የአሁኑን ሸጋ መንግሥት ይጠላሉ
ከዚህኛው መንግሥት
በፊት የነበሩትን ሳይቃወሙ ይህንን መንግሥት ብቻ ተቃውመዋል በማለት ተቃውሟቸውን ለአሁኑ መንግሥት ጥላቻ ስላላቸው ነው የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰሃል።
ምናልባት
ፓለቲካና ኮረንቲ በሩቁ እንል ከነበርነው መኻል ሆነህ ይሆናል እንጂ የቀደሙትንም መንግሥታት የሚቃወሙ ኦርቶዶክሳውያን ነበሩ።የአሁኑን መንግሥት ስለመቃወማቸው በቂ ምክንያት የላቸውም ካልክ ሞግታቸው።የሠራውን መልካም ሥራ ለማጨናገፍ ነው ካልከም ተከራከራቸው። በበኩሌ መገደላችንን ያስቁምልን ብለው ለመንግሥት በመጮኻቸው መንግሥትን ነኩብኝ ብዬ በመቀየም የአርሲ ኦርቶዶክሳውያንን መገደል ከማውገዝ ግን አልመለስም።
ከዚሁ ጋር አያይዘህ (ባለፈው ግዜ በነነዌ ጾም ሞዴልነት መጾማቸውንና ጥቁር መልበሳቸውን መሆኑ ነው መሰለኝ) በመንግሥት ላይ የአመጽ ቅስቀሳ አድርጋችኋል ብለሃቸዋል። ጾም ማወጃቸውና ጥቁር መልበሳቸውን ግን እንደ እምነታቸው ስለአገሪቷ ንስሐ መግባታቸውና መከራው እንዲቀር መጸለያቸው ነበር እንጂ አንተ እንዳስመሰልከው በመንግሥት ላይ የአመጽ ጥሪ አልነበረም።በንስሐ ሥርዐቱ ላንስማማ እንችላለን። የድርጊቱን ዐላማ ማዛባት ግን አይገባም።
እርግጥ እንዲያ እንዲሆን የሚፈልጉ የመንግሥት ተቃዋሚዎች አልነበሩም ብዬ መናገር አልችልም።ከእነዚያ ወገኖች አንዳንዶቹ ፣ "ያኔ አመጽ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ ቤተክርስቲያን እስከ አሁን ከችግሯ ትላቀቅ ነበር" ብለው በቁጭት የሚናገሩ ሰምቼአለሁ። ከጥቁር መልበሱ ጋር ሌሎች የማወኪያ ዘዴዎችን የዘረዘርካቸውም የሽርደዳ ንግግር እንጂ እውነትነት ያላቸው አይመስሉም።
አስከትለህ እንዳውም ውንጀላውን ሰቀልከው። መሪዎቹ የወጡበትን የከበረውን የኦሮሞ ሕዝብ ስሙን ያጠለሻሉ በማለት አስተያየትሀን መንግሥትን ከመጥላት ሕዝብን ወደመጥላት ከፍ አደረግኸው።
አርሲን
የምታውቀው ከሆነ በዚያ ያሉ ኦርቶዶክሳውያን አማራ ተብለው ስለሚጠሩና (እስከማውቀው ድረስ) አማሮች ተገደሉ መባሉ ይህን እንድትል አድርጎህ ከሆነ አላውቅም። ገዳዮቹም አማራ ገደልን ሰለሚሉ ኦሮሞ ተወቃሽ እንደተረገ መስሎህ ይሆናል።
በእርግጥ
ኦርቶዶክሳውያኑ አማራ ተብለው እስከተጠሩ ፣ የሚገደሉትም አማራ ተብለው እስከሆነ ድረስ ከአማራ ተጋዳዮች ጋር እንዲሰለፋ የሚያሳስቡ አሉ። እነዚያ ኃይሎች አማራ በሃይማኖት ፥ በመኖሪያ አካባቢና በመሳሰለው ውስጥ የመጋደል አቅሙን ከሚያስቀምጥ፣ ኃይሉን በአንድ ላይ በአንድ አማራነት ከረጢት ቢያስቀምጥ ተቃውሞው ውጤታማ ይሆናል ብለው ይወተውታሉ። መንግሥትም በበኩሉ እጁን አጣጥፎ አልተቀመጥም።አብረውት ከሚሠሩ ጋር በመሆን ይህ እንዳይሆን አስከሪን ቆጠራውን በዘር እየሽነሸነ ያቀርባል (በነገራችን ላይ ይህን የአስከሬን አቆጣጠር ዘይቤ ያስተማሩን ገና ሥልጣኑ ላይ ብዙም ሳይቆዩ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነበሩ)።የሌሎች ሃይማኖት ሰዎችም ተገድለዋል በማለት ጥያቄውን ለማፋዘዝ ይተጋል። ታዲያ በዚህ መኻል የኦሮሞን ማሕበረሰብ የሚያስወቅስ ምን ንግግር ታየህ? የአኦሮሞ ማኀበረሰብን የሚነካ ነገር የለበትም። ሊነካም አይገባም።
ባይሆን
ጉዳዩ የተፈጸመው በኦሮምያ ክልል ስለሆነ የኦሮሚያ ስሙ ጠፋ የሚለው ወቀሳ ያስኬዳል። ለዚህ መድኅኒቱ "በጎ ነገር ሲደረግ ኦሮምያ ክልል፥ ክፋ ሲደረግ ግን ክልል 4 እያሉ መናገር ይሻል ይሆን? እላለሁ።ለማንኛውም በአርሲ ኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰባቸው በደል ከተገመተው ስም ማጥፋት ጋር ስመዝነው ዝም እንድል አያደርገኝም።
7. በሰሜንም በደቡብም ላለው አድልዎ ሳናደርግ እንቆረቆራለን
ዘርና
ሃይማኖት ሳንመርጥ ለሰው በሰውነቱ ብቻ እንጮህለታለን ያልከው የከበረ እንቁ ነው።ታዲያ እንዲህ ለሰው ሁሉ ከገደደህ ምነው የአርሲ ኤርቶዶክሳውያን ተገዳዮችን መጨመር ተናነቀህ? አልፈህ ተርፈህ ሌሎቹንም አትጩሁላቸው አልክሳ!” ለሚልህ ምን መልስ አለህ? መሙለጭለጪያ ብልሃት ሆኖ ይታየኛል። ለሁሉ መቆርቆር ሸጋ ነገር ሆኖ ሳለ የሚመርጡትን ለመደገፍና ቸል የሚሉትን ለመዝለል እንደ ሰበብ ሲገለገሉበት ግን አባ ጨጓሬ ነው።
መደምደሚያ
ፓስተር
እንደመሆንህ መጠን የበጎች መጎዳትና ጥበቃ ጉዳይን ትረዳለህ/ትገነዘባለህ ብዬ አምናለሁ።የፓስተር ቅድሚያ ኅላፊነት መንግሥትን መጠበቅ ሳይሆን በጎችን መጠበቅ እንደሆነ የምታጣው አይመስለኝም።በእርግጥ መንግሥትና መንጋው አንድ ሆነው ሲታዩ ሁለቱንም የመጠበቅ ኃላፊነት ሊሰበጣጠር ይችላል።የኦርቶዶክሳውያን ስለበጎቻቸው የሚያሰሙትን አቤቱታ እንደ እረኛ ሆነህ በማሰብ ርኅራኄን እንደምታሳያቸው ተስፋ አደርጋለሁ።ደግሞም በቪዲዮ እንዳየሁህ አዲስ ነገር ለመማር የሚችል ዕድሜ ላይ ያለህ ስለሚመስል ፈጥነህ ይኽን ትገነዘባለህ ብዬ አምናለሁ።
እኔ ግን ኦርቶዶክሳውያን አትግደሉን ማለታቸውን አታስተጋቡ /አታሽቃብጡ ያልከውን ምክር ወይም ተግሣጽ ለመቀበል ከላይ እንዳተትኩት ምክንያቶቹ በቂ ሆነው አላገኘኋቸውም። ስለዚህ እምቢታዬን በታላቅ ትህትና እንድገልጽ ይፈቀድልኝ።
አዎ
መንግሥት ኦርቶዶክሳውያንና ሌሎች ሰላማዊ ዜጎችን (አማራውን ጨምሮ፥ በማንኛውም ትርጉም) ያለ ሥጋት ከአንዱ የኢትዮጵያ ጫፍ ወደ ሌላው የኢትዮጵያ ጫፍ መዘዋወር እንዲችሉ እንዲሁም የትም መኖርና መሥራት እንዲችሉ ጥበቃ ያድርግላቸው።
እንዳሁኑ
መንግሥት ኦርቶዶክሳውያኑን ጨምሮ ሕዝብን የመጠበቅ ኃላፊነቱን በብቃት ሳይወጣ ሲቀር ይወቀስ/ይጠየቅ።ሕዝብ በኃላፊነት የሚጠይቀው ገዳዮቹን ሳይሆን መንግሥትን ነውና።
ወንድሜ
ፓስተር ግርማ ቤካ:-”በነገር ሁሉ እንዲከናወንልህ፥ ጤና እንዲኖርህ” እመኝልሃለሁ። ደህና ሁንልኝ። ቸር እንሰንብት
በጌታ
ወንድምህ ባንቱ ገብረሚርያም
Comments
Post a Comment