መርጠው ያልቅሱበት
መጀመሪያ መርጦ የማልቀስ ምሳሌዎች ናቸው ያልኳቸውን ልጻፍ፦
*ለወንጌላውያን የቀብር ቦታ አይከልከል፣ ለሁሉም ይፈቀድላቸው!
*የሽርካ ኦርቶዶክሳውያንን መግደል ይቁም!
*የኩሪፍቱ ቃለ ሕይወት ማዕከል አይወሰድ!
*በዝቋላ መነኮሳት ግድያ መፈጸሙ አሰቃቂ ነው፣ ወንጀለኛው ይታወቅ፤ ይቀጣም!
*በምዕራብ የአገራችን ክፍል የመሠረተ ክርስቶስ አባላትን የገደሉ ይያዙ፣ ይቀጡ!
*በዚያው ዞን የመካነ ኢየሱስ ምዕመናንን ከጸሎት ሥፍራ ወስደው የገደሉ ይያዙ፣ይቀጡም!
*ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር አብይ ኃላፊነታቸውን በሚገባ አልተወጡምና በኃላፊነት ይጠየቁ!
*ለሰላማችን መጥፋት ምክንያት ነውና አሸባሪዎች ስለ አመጽ ሥራቸው ይወገዙ!
*ታዬ ደንደአ መታሰሩና ቤተሰቡ ለችግር መዳረጉ ፍትሐዊ አይደለም! ይለቀቅ!
*እውነትን ስለተናገሩ አቶ ታዲዎስ ታንቱን ማሰሩ ሕገወጥ ድርጊት ነው ይፈቱ!
*በምሥራቁ የአገራችን ክፍል ታሪካዊው የመካነ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን ሕንጻ አይወረስ! ወዘተርፈ
መርጦ ማልቀስ የሚባለው እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉትን ጥያቄዎች ችግሮቹ እንደተከሰቱ መጠየቅ መስሎኛል። ካልሆነ እታረማለሁ። ታዲያ እንዲህ ዐይነቱን ጥያቄ አትጠይቁ የሚሉ የተከበሩ ዎገኖችን በየዩትዩቡ ተመልክቼአለሁ።
በደፈናው “የኢትዮጵያውያን ሰላም፣ እኩልነትና ነጻነት ይረጋገጥ በሉ! መርጣችሁ አትጠይቁ” ማለታቸው ሆኖ ተሰምቶኛል። እንዳውም ችግር እንደተከሰተ ስለዚያ የሚጠይቁትን ፣ በሽሙጥ “መርጦ አልቃሾች” የሚል ስም በመለጠፍ “ዐይነ አፋር” ሊያደርጓቸውም ይሞክራሉ።ይህን ሲያደርጉ “የሰው ሁሉ አፍቃሪ ፣ መልካም ሰዎች፣ አድልኦ እማያውቃቸው” እንደሆኑ ስለራሳቸው ሳይሰማቸው አይቀርም» መርጦ ድጋፍ መስጠትን “ከፉፉይ ዐሳብ” የሚያደርጉትም ይመስላል።
ለእኔ ግን “መርጣችሁ አታልቅሱ” ማለት “ለማንም አታልቅሱ!” የማለት ያህል ኃላፊነት የመሸሽ ብልሃታዊ አነጋገር ሆኖ ይሰማኛል። “መርጦ አጥቂና መርጦ አበልጻጊ” እስካለ ምን ማድረግ ይቻላል? በቃ መርጠው ያልቅሱበት፣ እንተዋቸው። “ለሁሉም ነው የምንቆረቆረው” የሚሉም ይሻላል እስካሉ ድረስ “አድበስብሰው” ያልቅሱ።ሆኖም አድበስባሾቹን መጠርጠር አይቻልም ትላላችሁ? ለውጥ እንዲመጣ የማይፈልጉ እንዳይሆኑ?
Comments
Post a Comment