“የአቤል ደም” እና “አብረን ሰው እንሁን”
መግቢያ
የ“አቤል ደም” ጸሐፊ አባ ጴጥሮስ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ሲሆኑ ፤ የ”አብረን ሰው እንሁን” ጸሐፊ ደግሞ ሰለሞን ጥላሁን (ፓስተር) የኢትዮጵያ ወንጌል አማኝ ነው።
የ"አቤል ደም" በእጄ የገባው በመሸጪያ ድንኳኑ ፊት ለፊት ሰልፍ አይቼ ፣ “ምን ቢሆን ነው” በማለት ሰልፉን ተቀላቅዬ ነው (በአትላንታው በአሜሪካ የኢትዮጵያውያን እስፖርትና ባህል በዐል ላይ ማለት ነው)።“አብረን ሰው እንሁን”ን ያገኘሁት አንድ ወዳጄ ልኮልኝ ነው (በዚህ አጋጣሚ ፓስተር ሰለሞንን አንድ ቅጂ ደርሶኛል አመሰግናለሁ ማለት እወዳለሁ)።
የአቤል ድምጽ እጄ ከመግባቱ ከሁለት ሳምንት ቀደም ብዬ “አብረን ሰው እንሁን”ን አንብቤው ነበር። የጽሑፌ ርዕስ ይኸንኑ የንባቤን ቅደም ተከተል (ከፊት ወደ ኋላ) የሚያንጸባርቅ ነው።
የመጽሐፍ ሐያሲ አይደለሁም። የምጽፈው ለማሔስ አይደለም፣ የተጻፈው ሁሉ ገብቶኛል፣ ዘልቄዋለሁ ብዬም አይደለም።ለወገኑና ለአገሩ ችግር መፍትሔ ተገኘ ብሎ ሰፍ እንዳለ ሰው በ"ፈጣን ንባቤ" ከመጽሐፎቹ የጨበጥኩትን ያህልና የተሰማኝን ለማካፈል ነው። በሳትሁትና በተሳሳትሁት ለመታረምና ለመማር ዝግጁ ነኝ
ከመጽሐፍቱ የተማርኩት
ሁለቱም መጽሐፎች በርካታ ገጾች በመያዛቸውና ዐሳቦቹም ለእኔ አዲስ በመሆናቸው በማነብበት ወቅት በማስመር፣ በማድመቅ፣ በማክበብና በጥያቄ ምልክት ሞልቼአቸዋለሁ።
ያለጥርጥር እጅግ ብዙ የተደከመባቸው ናቸው።በንባቤ እንደተረዳሁት ከሆነ ሁለቱም ጸሐፊዎች “እኛን ኢትዮጵያውያንን ሰው እንሁን” ብለው ጋብዘውናል። የአቤል ደም ጸሐፊ “ሰው” የሚሉት አስተሳስቡና አካሄዱ በገነት ከመውደቁ በፊት ወደ ነበረው ክብሩ የተመለሰውን እንደሆነ ተሰምቶኛል።“አብረን ሰው እንሁን” ደግሞ “ ሰው” ማለቱ በንኡስ ማንነት (ጾታ፣ ቀለም፣ ብሔር ወዘተርፈ) ከመውረድ ወጥቶ ትልቅ ማንነቱ ማለትም “”መለኮት ሰጥ” የሆነ ክብር ያለውን ማለቱ እንደሆነ ተሰምቶኛል።
የአቤል ደም ጸሐፊ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የደረሰው ጉስቁልና ፣ ግፍ፥ ሰቆቃና መሪር ጩኸት እንዳመመው፣ እንደ አስለቀሰውና እንዳሳስበው እረኛ የጻፋት ነው።በለቅሶ ስሜት ታጭቋል።የአብረን ሰው እንሁን ጸሐፊ ግን ስለ ግጭቶች ያለውን ሳይንሳዊ ዕውቀት የተነተነበት ነው።
“የአቤል ደም” ጸሐፊ አግባብ ባለው ሥፍራ ሁሉ “ቃየል” በሚሏቸው (የመንግስት፣ የፖለቲካ እና የቤተክርስቲያን ኅላፊዎች) ላይ ብስጭታቸውንና ወቀሳቸውን ሳያሰሙ አያልፉም። እንዲሁም እንደ “አቤል ደም” ጩኸታቸው ወደ እግዚአብሔር ወጥቷል ለሚሏቸው በከንቱ ደማቸው ለፈሰሰውና ለሚጎሳቆሉት (ለግፉአን) ምስኪን ኢትዮጵያውያን ሃዘነቴያቸውን፣ ርኅራኄያቸውን፣ ቁጭታቸውንና ዕንባቸውን ሳያፈሱ አያልፉም።
የሰላም መንገዱ (ከጉዳት መውጨያው)፦- ንስሐ መግባት (በንባቤ እንደገባኝ ኃጢአትን/በደልን /ጉዳትን ማወቅ ማለት ነው፟)--- መናዘዝ (ሰበብ ሳያበዙ ስለበደሉ ኅላፊነትን መውሰድ ማለት ነው)-ኃጢአቱን መተው/መመለስ----ይቅርታን ማግኘትና መስጠት (ቂምን፣ በቀልን መተው ማለት ነው)- እርቅ ማውረድ (የሁለት ወገን መስማማት ማለት ነው) እንደሆነ አስምረውበታል። እነዚህ ምን ማለት እንደሆኑና እንዳልሆኑ ፣ዐይነታቸውን፣ እንዴት እንደሚከናወኑ፣ ተግዳሮቶቻቸው ምን እንደሆኑ ፣ እንዴት እንደሚሰላሰሉ ወዘተርፈ ዝርዝር ዕውቀት አካፍለዋል።
በማሳያነት፣ በማረሚያነት፣በማበረታችነት፣ በአስረጂነት፣ በአርአያነት ከመጽሐፍ ቅዱስ በርካታ ታሪኮችን እንደ አገባቡ እየጠቀሱ የንስሐ፣ የይቅርታና የእርቅ ጉድዮችን ያፍታታሉ፣ ያብራራሉ። በመስኩ የስመጥር ጸሐፊዎችን ዕውቀትም (ለጸሓፊዎቹ እውቅና በመስጠት) ከመጽሐፍ ቅዱስ ካገኙት ትምህርት ጋር በማዛመድ መልዕክታቸውን አጠንክረው ገምደውታል።አልፎ አልፎ የተረኩት ዛሬ ላይ የሚታወቁ ሰዎች ታሪኮችም የግል ሕይወትን ይበረብራሉ።ለንስሐችን፣ ለይቅር መባባላችንና ለዕርቃችን ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ የተሠራው ሥራና ትምህርቱ መሠረታችንና ምሳሌያችን መሆኑን አጽንኦት ሰጥተውታል።
ለዘለቄታዊ ሰላም ማንኛውም ወገን ሥርዐተ እምነቱን (value system) እግዚአብሔርን ማዕከል ያደረገ (theocentric) ፣ ፈሪሐ እግዚአብሔር ያለው (እንደገባኝ በእግዚአብሔር መታመንና እግዚአብሔር የሚደሰትበትን ፈቅዶ ማድርግ፣ የማይደሰትበትን ከማድረግ ቆርጦ መራቅ ነው) ወደ ማድረግና መሆን እንዲመለስ ይመክራሉ።
አብረን ሰው እንሁን ጸሐፊ ደግሞ ግጭት ልውጠታዊ (ከአባ ኮስኳሴ ቢራቢሮ እንደሚወጣ እንዳለው) ሊሆን እንደሚችልና እንዴት እንደሚደረግ፣ ሰላምም የሚገነባ ጉዳይ እንደሆነና እንዴት እንደሚገነባ እንዲሁም ስለ ግጭት ተያያዥ ጉዳዮችን አሳምሮና ከሽኖ ተንትኗል፣ አስተምሯል። በየሥፍራው የሰጠው ዕጣሬና የግንዛቤ ጥያቄ (አንዳንዴ ለአንዱ ምዕራፍ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ለሁለት ምዕራፎች አያጣመረ) መጻፉ ዐሳቡን ለመከለስና ለማሰላሰል የሚጋብዝ ነው። አንባቢዎቹ ዐሳቡን እንደተረዱለት እርግጠኛ ለመሆን ያደረገው ጥረት ሆኖ ተሰምቶኛል። ጥንቅቅ ያለ አቀራረብ ነው።
ሁለቱም ጸሐፊዎች (በተለይ የ”አብረን ሰው እንሁን፡ ጸሐፊ”) ለመዳበሩ እንዲሆን ዐማርኛ ቋንቋን ሆን ብሎ ዐልሚ ምግብ መግቦታል።
የራሴ ድምዳሜ፦ የአቤል ድምጽ ማዕከሉ (በአመዛኙ ለማለት ነው) ለልባችን፣ የ"አብረን ሰው እንሁን” ደግሞ ማዕከሉ ለአእምሯችን መናገር ሆኖ ከሚታይ በስተቀር ሁለቱም ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን የሚገዳቸው መሆኑ በግልጽ ይነበባል። ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንዳሰቡለት «እግዚአብሔር ያስብላቸው ፣ ሰሚ ይስጣቸው!»እላለሁ።፣
በተያያዘ፦ በወንጌላውያን የተጻፋትን ኦርቶዶክሳውያን ፥ በኦርቶዶክሳውያን የተጻፋትን ወንጌላውያንን ቢያነቡ ይጠቅም ይሆን? በዚህ ርዕስ ላይ ከሙስሊም ወገኖች የተጻፈ ካለ ለማንበብ አልቦዝንም።
እግዚአብሔር ይስጥልኝ። ቸር እንሰንብት
ባንቱ ገብረማርያም
ይህን ከለጠፍኩ በኋላ የ"አብረን ሰው እንሁን" ጸሐፊ ከዚህ ዓለም ድካም ማረፉን ሰምቼ አዝኛለሁ። ለመላው ቤተሰቡ መጽናናትን ይስጥልኝ።
Comments
Post a Comment