የማርያምን ሥዕል ስለቀደደችው፡
አድማጭ ተመልካቾቼ፡ እንደምን አላችሁ? እኔ ደህና ነኝ።
ሰሞኑን የማርያም ሥዕል መቀደዱን ከማህበራዊ መገናኛ ተመለከትኩ። ስለዚያ ያለኝን አስተየየት እንደሚከተለው አቀርባለሁ። እንድትከታተሉት በታላቅ ትህትና እጋብዛችኋለሁ።
በመጀመሪያ ስለ ማርያም ሥዕል ያለኝን አንድ ትውስታ ልንገራችሁ። በጎባ/ባሌ የአዝማች ደግልሃን ት/ቤት ተማሪ ነበርኩ (ስሙ ተቀይሯል)። ይህ ታሪክ የሆነ ጊዜ የስንተኛ ክፍል ተማሪ እንደነበርኩ አሁን ተዘንግቶኛል። የዘጠነኛ ወይም የአሥረኛ ክፍል ተማሪ የነበርኩ ይመስለኛል። በዚያን ዐመት በትምህርት ቤቱ የተማሪ ክበቦች ተቋቁመው ነበር።ታዲያ እኔም ከተቋቋሙት አንዱ ከነበረው ከመጽሐፍ ቅዱስ ክበብ ገባሁኝ። የክበቡ መሪ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዩኒቨርስቲ (ስሙ ተቀይሯል) በብሔራዊ አገልግሎት የመጣ የኬሚስትሪ አስተማሪ ነበር። አንዱን ቀን መጽሐፍ ቅዱስን ሊያስተምረን አባላቱን ሚካኤል ጋራ ላይ ይዞን ወጣ። (አካባቢውን ለማታውቁት ሚካኤል ጋራ ከትምህርት ቤቱ ጀርባ የተቆለለ ጋራ ነው)። እዚያ ስብሰባ ላይ ነበር የማርያምን ሥዕል ያደለን።የሥዕሉ ትልቅነቱ የኪስ ቦርሳ ውስጥ ለማስገባት የሚያስቸግር ያህል ነበር።እጅግም ትልቅ አልነበረም ለማለት ነው። ት/ቤት ለዕረፍት በተዘጋበት ጊዜ ያንን ሥዕል ይዤ ጎሮ ወረድኩ።ለእናቴ ሰጠኋት። እጅግ በጣም ደስ አላት። እያገላበጠች ሳመቻት። በኋላም የክት ልብስ በሚቀመጥበት ሳጥን ውስጥ ሥዕሏን በጥንቃቄ አስቀመጠችው። መረቀችኝ። ያ ቀን እናቴን ደስ ያሰኘሁበት የማይረሳኝ አንዱ ቀን ነበር።
ይህን ትውስታዬን የቀሰቀሰው ሰሞኑን የማርያም ሥዕል በአደባባይ መቀደዱ ነው።እናቴ ዛሬ በሕይወት ኖራ፣ የማርያም ሥዕል ተቀደደ መባልን ብትሰማ፣ ምን ያህል ታዝን እንደነበር ታየኝ። የመደባደብም ሆነ የመሰዳደብ ነገር የማይታይባት ስለነበረች፣ ምናልባት የቀደደችው ሰው ትደብደብ አትልም ይሆናል። ነገር ግን በጣም እንደምታዝንና በነጠላዋ ጫፍ እንባዋን እየጠራረገች እንደምታለቅስም ታየኝ። የብዙ እናቶች ስሜትም ተመሳሳይ የሚሆን ይመስለኛል።
ታዲያ ይህን አስቤ፦ “የማርያምን ሥዕል የቀደደችዋ ልጅ ምነው ይህን ዐይነት ደስታ ለመስረቅ ምክንያት ባልሆነች? ምን ረብ ኖሮት ቀደደች? እናቶችን የሚያሳዝን ነገር ምነው ባልመረጠች” ብያለሁ። “እንዳው ለመሆኑ ለምን አደረገችው?”፤- ያስከተልኩት ጥያቄ ነበር።በዚህ ድርጊቷ ሥዕሉ አንዳች የማድረግ ኃይል የለውም ብላ መልዕክት ለማስተላለፍ ፈልጋ ከነበረ መልዕክቱ ለማነው? ኃይል የለውም የምንል እንደሆንን አለማመናችንን ለማስረገጥ ወይም ለማጽናት ይህ “ዴሞ” “ማሳያ“ አያስፈልገንም። ሥዕሉን ከመቅደዷ ጋር አንድ ነገር ተከትሎባት የነበረ ቢሆን እንኳ ማፋረሻ ምክንያት እናገኝለት ነበር እንጂ በዚያ ምክንያት አለማመናችንን እንቀይር የነበር አይመስለኝም።
"ሥዕለ አድኖ" (በትክክለኛው ሆኅያት ያልጻፍኩ ከሆነ ይቅርታ) ነው ብለው የሚያምኑት ኦርቶዶክሳውያኑ ደግሞ ልጅቷ ቀድዳ አንዳች ነገር ባለመሆኗ “እውነትም ማርያም ኃይል የላትም” ብለው እምነታቸውን አይጥሉም።
ታዋቂ መሆን ፈልጋ ከሆነ ብቻ ተሳክቶላታል። ደፋርነቷንና ኅይለኝነቷን በአደባባይ ለማሳየት ከሆነም ምናልባት ተሳክቶላት ይሆናል (ይህ ቁምነገር ከሆነ)። በአሁኑ ዘመን አንዱ የሥራ መስክ በዩትዩብና በቲክ ቶክ የሚቀርብ ነገር ማዘጋጀት ነውና ለዚያ እንዲሆናት አስባም ሊሆን ይችላል።ብቻ ለምን ዐላማ እንዳደረገችው የምታውቀው እርሷ ነች።
ለእኔ ግን ምን ሊሆን እንደሚችል ለመገመት አስቸግሮኛል። በዚህ ድርጊቷ ሰዎችን ወደ እኛ እምነት (በድምሩ ወደ ወንጌላውያኑ) ለማፍለስ ያሰበች ከነበረም ፣ የእምነት ምልክቱን ከመቅደድ ይልቅ “በግላችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ፣ ከቤተሰብ በተቀበላችሁት ልማድ አትተማመኑ” ዐይነት ነገር ብትናገር የተሻለ የነበረ ይመስለኛል። ያደረግሁት “ለጌታ ቀንቼ ነው” ብላ ጥቅስ መጥቀስ ትችል ይሆናል። የተዋስኩትን አባባል ልጠቀምና፡ - “ውሃ አይቋጥርም”። በእርግጥ ውይይትን ተንኩሷል። ይህ ደግሞ የጎንዮሽ ጥቅም እንጂ እርሷ አስባበት ያስከተለችው አይመስለኝም።
በድርጊቷ የተቆጡባት ብዙ ኦርቶዶክሳዉያን እንዳሉ ከማኅበራዊ ሚዲያው ተከታትዬአለሁ። አንዳንዶቹም በአካል ጉዳት ሊያደርሱባት እንደሞከሩ ሰምቼአለሁ።ልጅቷ ያደረገችው ዐይነት የአደባባይ አመጽ፣ የመጠቃትና የመደፈር ስሜት ስለሚያሳድር በመቆጣታቸው አልተደነቅሁም። በተለይም በጴንጤዎች በራሳቸው ወይም በጴንጤዎች ስም በተደጋጋሚ ተዘልፈናል፣ ጉዳት ደርሶብናል፣ በሚሉበት ዘመን ላይ በእሳት ላይ ቤንዚን እንደማርከፍከፍ እንደሚሆን እገምታለሁ። በሆደ ባሻነታቸው ላይ የተደረገ መሆኑን እገነዘባለሁ። ያማል!! ያለጥርጥር ስሜት ይጎዳል!! ይሁን እንጂ ልጅቷን በአካል መጉዳትን አስቀርተው ስለ "ስዕለ አድኖ" ለማስረዳት፣ ለማስተማርና ለመመከት አጋጣሚውን ለመጠቀም ሊመርጡ ይችላሉ።
ስለተከታተላችሁኝ አመሰግናለሁ።
ማርያምን የማክበር ጉዳይ ለምን ይህን ያህል እንደሚያውክ፣ ምን እንደተገኘበት አልገባህ ይለኛል።
ደህና ሁኑልኝ።
Comments
Post a Comment