Skip to main content

የማርያምን ሥዕል ስለቀደደችው፡

 የማርያምን ሥዕል ስለቀደደችው፡

አድማጭ ተመልካቾቼ፡ እንደምን አላችሁ? እኔ ደህና ነኝ።

ሰሞኑን የማርያም ሥዕል መቀደዱን ከማህበራዊ መገናኛ  ተመለከትኩ። ስለዚያ ያለኝን አስተየየት እንደሚከተለው አቀርባለሁ። እንድትከታተሉት በታላቅ ትህትና እጋብዛችኋለሁ።

በመጀመሪያ  ስለ ማርያም ሥዕል ያለኝን  አንድ ትውስታ ልንገራችሁ። በጎባ/ባሌ የአዝማች ደግልሃን ት/ቤት  ተማሪ ነበርኩ (ስሙ ተቀይሯል)። ይህ ታሪክ የሆነ ጊዜ የስንተኛ ክፍል ተማሪ እንደነበርኩ አሁን ተዘንግቶኛል። የዘጠነኛ  ወይም የአሥረኛ  ክፍል  ተማሪ የነበርኩ ይመስለኛል። በዚያን ዐመት በትምህርት ቤቱ  የተማሪ ክበቦች ተቋቁመው  ነበር።ታዲያ እኔም ከተቋቋሙት አንዱ ከነበረው ከመጽሐፍ ቅዱስ ክበብ  ገባሁኝ።  የክበቡ መሪ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዩኒቨርስቲ (ስሙ ተቀይሯል) በብሔራዊ አገልግሎት የመጣ የኬሚስትሪ  አስተማሪ ነበር። አንዱን ቀን መጽሐፍ ቅዱስን ሊያስተምረን አባላቱን  ሚካኤል ጋራ ላይ ይዞን ወጣ። (አካባቢውን ለማታውቁት ሚካኤል ጋራ ከትምህርት ቤቱ ጀርባ የተቆለለ ጋራ ነው)። እዚያ ስብሰባ ላይ ነበር የማርያምን ሥዕል ያደለን።የሥዕሉ  ትልቅነቱ  የኪስ ቦርሳ ውስጥ ለማስገባት የሚያስቸግር ያህል ነበር።እጅግም ትልቅ አልነበረም ለማለት ነው። ት/ቤት  ለዕረፍት በተዘጋበት ጊዜ  ያንን ሥዕል ይዤ ጎሮ ወረድኩ።ለእናቴ ሰጠኋት። እጅግ በጣም ደስ አላት። እያገላበጠች ሳመቻት። በኋላም የክት ልብስ በሚቀመጥበት ሳጥን ውስጥ ሥዕሏን በጥንቃቄ  አስቀመጠችው። መረቀችኝ። ያ ቀን እናቴን ደስ ያሰኘሁበት የማይረሳኝ አንዱ ቀን ነበር። 

ይህን ትውስታዬን የቀሰቀሰው ሰሞኑን የማርያም ሥዕል በአደባባይ መቀደዱ ነው።እናቴ ዛሬ በሕይወት ኖራ፣ የማርያም ሥዕል ተቀደደ መባልን ብትሰማ፣ ምን ያህል ታዝን እንደነበር ታየኝ። የመደባደብም ሆነ የመሰዳደብ ነገር የማይታይባት ስለነበረች፣ ምናልባት የቀደደችው ሰው ትደብደብ አትልም ይሆናል። ነገር ግን በጣም እንደምታዝንና  በነጠላዋ ጫፍ እንባዋን እየጠራረገች እንደምታለቅስም ታየኝ። የብዙ እናቶች ስሜትም ተመሳሳይ የሚሆን ይመስለኛል።

ታዲያ ይህን አስቤ፦ “የማርያምን ሥዕል የቀደደችዋ ልጅ ምነው ይህን ዐይነት ደስታ ለመስረቅ ምክንያት ባልሆነች? ምን  ረብ ኖሮት ቀደደች?  እናቶችን የሚያሳዝን ነገር ምነው ባልመረጠች” ብያለሁ። “እንዳው ለመሆኑ ለምን አደረገችው?”፤-  ያስከተልኩት ጥያቄ ነበር።በዚህ ድርጊቷ ሥዕሉ አንዳች  የማድረግ ኃይል የለውም ብላ መልዕክት ለማስተላለፍ  ፈልጋ ከነበረ መልዕክቱ ለማነው?  ኃይል የለውም የምንል እንደሆንን አለማመናችንን ለማስረገጥ ወይም ለማጽናት ይህ “ዴሞ” “ማሳያ“ አያስፈልገንም። ሥዕሉን ከመቅደዷ ጋር አንድ ነገር ተከትሎባት የነበረ ቢሆን እንኳ ማፋረሻ ምክንያት እናገኝለት ነበር እንጂ በዚያ ምክንያት አለማመናችንን እንቀይር የነበር አይመስለኝም።

"ሥዕለ አድኖ" (በትክክለኛው ሆኅያት ያልጻፍኩ ከሆነ ይቅርታ) ነው ብለው የሚያምኑት ኦርቶዶክሳውያኑ ደግሞ ልጅቷ ቀድዳ አንዳች ነገር ባለመሆኗ “እውነትም ማርያም ኃይል የላትም” ብለው እምነታቸውን አይጥሉም።

  ታዋቂ መሆን  ፈልጋ ከሆነ ብቻ ተሳክቶላታል። ደፋርነቷንና ኅይለኝነቷን  በአደባባይ ለማሳየት ከሆነም ምናልባት ተሳክቶላት ይሆናል (ይህ ቁምነገር ከሆነ)። በአሁኑ  ዘመን አንዱ የሥራ መስክ  በዩትዩብና በቲክ ቶክ የሚቀርብ ነገር ማዘጋጀት ነውና ለዚያ እንዲሆናት አስባም ሊሆን ይችላል።ብቻ ለምን  ዐላማ እንዳደረገችው የምታውቀው እርሷ ነች። 

ለእኔ ግን ምን ሊሆን እንደሚችል ለመገመት አስቸግሮኛል። በዚህ ድርጊቷ ሰዎችን ወደ እኛ እምነት (በድምሩ ወደ ወንጌላውያኑ)  ለማፍለስ ያሰበች ከነበረም ፣ የእምነት ምልክቱን ከመቅደድ ይልቅ  “በግላችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ፣ ከቤተሰብ በተቀበላችሁት ልማድ አትተማመኑ”  ዐይነት ነገር ብትናገር የተሻለ የነበረ ይመስለኛል። ያደረግሁት “ለጌታ ቀንቼ ነው” ብላ ጥቅስ መጥቀስ ትችል ይሆናል። የተዋስኩትን አባባል ልጠቀምና፡ - “ውሃ አይቋጥርም”። በእርግጥ ውይይትን ተንኩሷል። ይህ ደግሞ የጎንዮሽ ጥቅም  እንጂ እርሷ አስባበት ያስከተለችው አይመስለኝም።

 በድርጊቷ የተቆጡባት ብዙ ኦርቶዶክሳዉያን እንዳሉ ከማኅበራዊ ሚዲያው ተከታትዬአለሁ። አንዳንዶቹም በአካል  ጉዳት ሊያደርሱባት እንደሞከሩ ሰምቼአለሁ።ልጅቷ ያደረገችው ዐይነት የአደባባይ አመጽ፣ የመጠቃትና የመደፈር ስሜት ስለሚያሳድር በመቆጣታቸው አልተደነቅሁም። በተለይም በጴንጤዎች በራሳቸው ወይም በጴንጤዎች  ስም  በተደጋጋሚ ተዘልፈናል፣  ጉዳት ደርሶብናል፣  በሚሉበት ዘመን ላይ በእሳት ላይ ቤንዚን እንደማርከፍከፍ እንደሚሆን እገምታለሁ። በሆደ ባሻነታቸው ላይ  የተደረገ መሆኑን እገነዘባለሁ። ያማል!!  ያለጥርጥር  ስሜት ይጎዳል!! ይሁን እንጂ ልጅቷን  በአካል መጉዳትን አስቀርተው ስለ  "ስዕለ አድኖ"  ለማስረዳት፣ ለማስተማርና ለመመከት አጋጣሚውን ለመጠቀም ሊመርጡ ይችላሉ። 

ስለተከታተላችሁኝ አመሰግናለሁ።

 ማርያምን የማክበር ጉዳይ  ለምን  ይህን ያህል እንደሚያውክ፣  ምን እንደተገኘበት አልገባህ ይለኛል።

ደህና ሁኑልኝ።



Comments

Popular posts from this blog

Comparative Theology የነገረ መለኮት ንጽጽር (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት)/ በብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ሲኖዳ ሳልሳዊ

 የነገረ መለኮት ንጽጽር  (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት): የወደደ  ሁሉ በነጻ እንዲጠቀምበት ተፖስቷል። ይሁን እንጂ መብቱ በሕግ የተጠበቀ ስለሆነ በየትኛውም መልኩ ለንግድ እንዲውል አልተፈቀድም። ልዩ ልዩ መግቢያ የሚለውን መጀመሪያ ካነበቡ በኋላ የተቀረውን በተመረጠው ቅደም ተከተል ማንበብ ይቻላል። ልዩ ልዩ መግቢያ   ጥምቀት   ትውፊት (ወግና ልማድ)   መካከለኝነት   ጾም የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ መንፈሳዊ ስጦታዎችና በልሳኖች የመናገር ስጦታ   ሥርዐት ንስሐ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ (1)  ድንግል ማርያምን ስለማክበር (2) ለጥያቄዎች መልስ (ሀ) ድንግሊትን ‘የወይን ግንድ (ተክል)’ና የ ‘ሕይወት በር’ የሚል ማዕረግ  ለምን እንሰጣታለን? (ለ) ወደ ድንግል ማርያም መጸለይ ትክክል ነው ወይ? (3) የድንግል ማርያም ድንግልና ዘላለማዊነት (4) ለተቃራኒ አስተያየቶች መልስ (ሀ) “የመጀመሪያ ልጇን” የሚለው ሐረግ (ለ) “ሚስትህ” የሚለው ሐረግ (ሐ) “አብረው ከመሆናቸው በፊት ጸንሳ ተገኘች” (መ) “የመጀመሪያ ልጇን እስክትወልድ አላወቃትም” (ሠ)  “ወንድሞቹ” የሚለው ሐረግ   የቅድስት ድንግል ማርያም  ክብሯ (1) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ድንግል እመቤታችንን አያከብሩም፤ ደግሞም እንድታማልድላቸውም (እንድትማልድላቸውም)  አይጠይቋትም።ከእነርሱ ወገኖች አንዳንዶቹ እንዲያውም ጫጩቱ ከተፈለፈለ በኋላ ዋጋ ከሌለው የዶሮ እንቁላል ቅርፊት ጋር እስከሚያመሳስሏት ይደርሳሉ።ይህ የተጋነነ ማቃለል የመጣው ምናልባት ሮሜዋውያን ካቶሊኮች የተጋነነ ማክበር ስለሚያከብሯት ለዛ ተቃርኖ ከማሳየት አዝማሚያ ሊሆን ይችላል። ስለዚህም ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን አንዱንም የእርሷን በዓል አያከብሩም።  (2) አንዳንዶቹ የፕሮቴስታንት ወገኖች ድንግል ማርያምን “እህታችን” ይሏታል። (3) በተጨማሪ አንዳንዶቹ ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ጌታ ኢየሱስን በድንግልና ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር ጋብቻዋን ፈጽማለች፤ የ‘ኢየሱስ ወንድሞች’  ወይም የ’ጌታ ወንድሞች’ ተብለው የተጠሩ ልጆችን ወልዳለች ይላሉ።  (4) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ቤተክርስቲያናችን ለድንግል እመቤታችን የሰጠቻቸውን አንዳንድ የማዕረግ ስሞችም ይቃወማሉ።  (5) ድንግልን ያለማክበራቸው አንዱ...

ከቄስ ( ዶ/ር ) ቶሎሳ ይልቅ

 አድማጭ ተመልካቾቼ አንደምን ከረማችሁ? የአብርሃም አምላክና አምላካችን የተመሰገነ ይሁንና እኔ ደህና ነኝ።"ከቄስ (ዶ/ር ) ቶሎሳ ይልቅ" በሚል ርዕስ ያዘጋጀሁትን  የሚከተለውን መልዕክቴን እንድትከታተሉልኝ በታላቅ አክብሮት እጠይቃችኋለሁ። ባንቱ ገብረማርያም ነኝ ከቄስ (ዶ/ር) ቶሎሳ ይልቅ           ቄስ (ፓስተር) ዶ/ር ቶሎሳ  ጉዲና የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን በአትላንታ/ጆርጂያ ፓስተር መሆናቸው በብዙዎች ዘንድ የሚታወቅ ይመስለኛል። በበኩሌ የማከብራቸውም ሰው ናቸው። በወንጌላውያን መኻል ለበርካታ ዐመታት ለኢትዮጵያ ሰላምና አንድነት የተናገሩ፣ ያሳሰቡና የጸለዩ መሆናቸውን ሰምቼአለሁ።በነገዳቸው የተደራጁትን የወንዛቸው ልጆችን ወቀሳ ተቋቁመው ለመላው ኢትዮጵያዊ ሲጮኹ የኖሩ ናቸው።           ስለ እሬቻ የሰጡት ትምህርት እስከዛሬ እንደሞዴል የማየው ነው። እሬቻን እንዳይከተሉና እንዳያስፋፉ የአሁኖቹን የመንግሥት ዐላፊዎች የመከሩበትንም ጊዜ አስታውሳለሁ።           የወንጌላውያን ሽማግሌ ብቻ ሳይሆኑ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ የአገር ሽማግሌ አድርጌ አያቸዋለሁ። ይህን መደላድል የማስቀምጠው ስለእርሳቸው ያለኝን አስተያየት ለማስታወቅና ይኸው ሐሳቤ የጸና መሆኑን ለማስጮህ ነው።አስተያየቴን አልጠየቁኝም፣ የሚጨምርላቸውም ሆነ የሚቀንስባቸው ነገር እንደማይኖርም ጠንቅቄ አውቃለሁ። መደላድሉን አስቀድሜ  ማስቀመጤ ወንድሞችንና እህቶችን “አይዟችሁ አትደንግጡ” ለማለት ያህል ነው። ...