ለዐማራ ብልጽግና ዐላፊዎች፦
እንደ ባሕላችንና እንደ ወጋችን አስድሜ የእግዚአብሔር ሰላምታዬን አቀረባለሁ።
ይኸንን ጽሑፍ አግኝታችሁ ለማንበብ ዕድል ላይኖራችሁ ይችላል። አግኝታችሁም መልስ የመስጠት ግዴታ አይሰማችሁ ይሆናል። እንደሰለጠነ አመራር ግን መረጃን ስታነፈንፉ ድንገት ታገኙታላችሁ ፤ መልስ ለመስጠትም አትቦዝኑም ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።
ጽሑፌን ከመቀጠሌ በፊት አቅሜን ልግለጥ። ምንም የፖለቲካ ሥራ ሠርቼ አላውቅም፣ ዕውቀቱም የለኝም። ስለዚህ የምሰጠው አስተያየት ለተቀማጭ ሰማይ ቅርቡ ነው ቢባል ሊያስኬድ እንደሚችል እገነዘባለሁ።አእምሮ እንዳለው ሰው ግን ማሰቤ አልቀረም።
በመጀመሪያ ሕዝብን ለማስተዳደር በመፍቀዳችሁ ላመሰግናችሁ እወዳለሁ። በተለይም በኢትዮጵያ ሁኔታ ይኸንን ለማድረግ በመምረጣችሁ መደነቅ የሚገባችሁ ይመስለኛል።
የልባችሁን የምታውቁት እናንተ ብትሆኑም ፣ ለማገልገል ገፊ ምክንያታችሁ የሚያስገኘው ክብር ወይም ጥቅም እንዳልሆነ ባምን ደስ ይለኛል።ኢሕዴን ሆናችሁ ብቅ ባላችሁበት ጊዜ ያ እንዳልነበረ ተመልክቼአለሁና። ወንበሩ ላይ ከተቀመጣችሁ በኋላ ግን እንደሚወራው ወሬ ከሆነ ያ ጠባያችሁ አልተቀየረም ብዬ ልሟገትላችሁ አልችልም።ኢሕዴን ሆናችሁ የሠራችሁትን ትክክል ነበር ወይም አልነበረም በማለትም ጉንጩን ለማልፋት አልሻም። አልፏልም፤ አይጠቅምም። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ብልጽግና እስከሆናችሁበት ጊዜም ለድርጅታዊ ነጻነታችሁ የውስጥ ትግል ስታደርጉ የቆያችሁ ይመስላል። አሁን የምጽፈው የዐማራ ብልጽግና ከሆናችሁ ወዲህ ስላለው ነው።
እሳቱ ላይ የተዳጣችሁት እናንተ ስለሆናችሁ አጣብቂኛችሁን የምታውቁትም እናንተ ናችሁ። እስካልተነፈሳችሁት ድረስ የማውቅበት ዘዴ የለኝም። ስለዚህ ጥያቄዬ ወይም አስተያየቴ በውጭ በምሰማው መረጃ ላይ ብቻ የተመሠረተ ነው።የውስጥ አዋቂ አይደለሁም። የውስጥ አዋቂም አላውቅም።ወሬው አሉባልታ ብቻ ከሆነ ይኸንኑ ትገልጡታላችሁ ብዬ አምናለሁ።
ከሌሎች የብልጽግና አባላት ጋር በመሆን መላዋን ኢትዮጵያ ስለምታስተዳድሩ ዘይቤያችሁን ለዚያ በሚስማማ መልክ ቃኝታችሁ
የዐማራ ሕዝብ ሆደ ሰፊነትና ሁሉን አቃፊነት ባሕል ጨምድዷችሁ
የመሪው ብልጽግና ክንፍ ተጽዕኖ በርትቶባችሁ
በሌላ ክልል ያለው ዐማርኛ ተናጋሪ ሕዝብ እንዳይጎዳ ተጠንቅቃችሁ
ሊሆን ይችላል፦ “ለቤት ቀጋ ለውጭ አልጋ” እንደሆናችሁ ይሰማኛል።በዚህ የአስተዳደር ዘመናችሁ የዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ እንዳልተመቸው አያለሁ።
በጅምላ ከመገደልና ከመቀበር ፣ ያለአግባብ ከመፈናቀል አልታደጋችሁትም። ወይም ራሱን እንዲከላከል ሁኔታን አላመቻችሁም (አልፎ አልፎ አንዳንድ ሙከራ እንዳለ ሰምቼአለሁ)።
በጦርነት ከመጠቃት የሚከለልበትን ዘዴ አላዘጋጃችሁም ነበር። ዛሬም ከዚያ ሥጋት አላወጣችሁትም።
በጠለፋ ከመወሰድና ከመሰወር አልታደጋችሁትም። የተጠለፉትንም መጨረሻ አልተከታተላችሁም
በመላዋ ኢትዮጵያ ተዘዋወሮ መሥራትና ንብረትን ማፍራት እንዲችል ዋስትና አላስገኛችሁለትም። ቀድሞ የነበረውንም የንብረት መብት አላስጠበቃችሁለትም።
እነዚህ የአንድ መንግሥት ትንሹና መሠረታዊ ኃላፊነቶቹ አድርጌ አያቸዋለሁ።አልተወጣችኋቸውም። ከዐማራ ክልል ውጭ የሚኖረው ዐማርኛ ተናጋሪ ፖለቲካዊ ውክልና እንዲያገኝ ማስቻልማ ቅንጦት ነው። “ጽድቁም ቀርቶ በጽድቁ በኮነነኝ” እንዲሉ፤ ይኼ ሁሉ ቀርቶ ጩኸቱን እንኳ ባደመጣችሁት ኖሮ።
ከዚህም የከፋው ለዐማራው ሕዝብ እንታገልለን ለሚሉት በሩንና መንገዱን መጠርቀማችሁ ነው። አልፎ ተርፎ እጃቸውን ትጠመዝዛላችሁ፣ ታስሯችዋላችሁ፣ ታጠፏቸዋላችሁ። ሲሆን ሲሆን የዐማራ ሕዝብን ሕልውና በማስጠበቁ አብራችሁ ልትተባበሩ በተገባችሁ ነበር።
ከክልሉ ውጭ ያለው ዐማርኛ ተናጋሪ በሰላም ሊኖር የቻለበት ሥፍራ የመኖሩም ምክንያት የእናንተ ሥራ ሳይሆን አብሮት የሚኖረው የአካብቢው ሕዝብ ክፉ መሥራትን አለመምረጡ ነው።
ስለዚህ የመተማመኛ ድምጽ ጠይቃችሁ የሕዝብ ዐመኔታ ካላገኛችሁ፣ በገዛ ፈቃዳችሁ ኃላፊነታችሁን "ለዐማራ ሕዝብ ሕልውና መጠበቅ" እንሠራለን ለሚሉ ለሌሎች ብትለቁና የእኛም ዕድል፣ የእነርሱም ችሎታ ቢሞከር እላለሁ።
ነው ወይስ እኛ በውስጥ ሥራዎችን ባንሠራ ኖሮ የባሰ ይሆን ነበር፤ ኃላፊነታችንን ከለቀቅን የዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ የባሰውን ሰማዩ ይደፋበታልና እንቀጥል ትሉኝ ይሆን?
የደፈርኳችሁ ዎገኔ ስለሆናችሁ ነው።እንደማትከፉብኝ ተስፋ አደርጋለሁ።
እግዚአብሔር ይስጥልኝ። ቸር እንሰንብት
Comments
Post a Comment