Skip to main content

አማትና ሥነ-ሥርዐት

 

አማትና ሥነ-ሥርዐት 

(ከMAY 2014 / REALSIMPLE.COM pp178-184)

(በጽሑፉ  የተመለከቱትን ጠበብት ማንነት ለማወቅ ለሚፈልግ በመጨረሻ ማስታወሻ ተሰጥቷል)

    በሚስቱና በእናቱ መኻል የሚኖረው ግንኙነት ብዙ ጊዜ ውጥረት የተሞላበት የሚሆነው ለምድነው? ስለዚህ የተወሳሰበ ግንኙነት አዲስ እይታና፣ ግንኙነቱን ለማሻሻል የሚረዳ ብልሃት አለ ወይ? የ”ሪይል ሲምፕል” መጽሔት አጠናቅሮ መልስ ይሰጣል።

    የሥነ ልቦና ባለሙያዋ ቴሪ አፕተር (2009) በአንድ ጥናታቸው ካካተቷቸው ሴቶች ከመቶዎቹ መኻል ስልሳዎቹ ምራት አማትን፣ አማትም ምራትን ‘ክፉ ነች’፣ ‘ቆሽቴን ታሳርረዋለች’ ፣ ‘አትመቸኝም’ በማለት የግንኙታቸውን ጎርባጣነት ገልጠዋል።

    ‘ሪል ሲምፕል’ መጽሔት አሰሳዊ ጥናትም ያሳየው ተመሳሳይ ነገር ነው። ስማቸውን ባልገለጡ 3700 ምራቶች እና 900 አማቶች ለ‘ሪይል ሲምፕል’ መጽሔት አዘጋጆች አማትና ምራት አንዳቸው ስለሌላቸው የሚሰማቸውን ገልጠው ነበር። የአሰሳ ጥናቱ በስድስት ጉዳዪች ዙሪያ ሲያጠነጥን ውጤቱ እንደሚከተለው ነበር።

  • አርባ ስምንት ከመቶ ምራቶች ጥርሳቸውን ለማስነቀል የጥርስ ሐኪማቸውን መጎብኘት ከሚፈሩት ይልቅ አማታቸውን መጎብኘት እንደሚፈሩ ተናግረዋል።
  • ምራት የምትበጠበጥበት ትልቅ ነገር አማቴ በጎ ዐሳቢ መስላ ትጎዳኛለች ማለቷ ነው።ሰላማዊና ደህና የሚመስለው የአማቷ ንግግር/ሥራ ያስቀይማታል።
  • አማት የምትበጠበጥበት ትልቁ ችግር ምራት ከባሏ ወላጆች ይልቅ ከራሷ ወላጆች ጋር የበለጠ ጊዜ ታሳልፋለች እና ለእነርሱ ታዳላለች፣ እኔን ታገለኛለች ብላ ማሰቧ ነው። አፐርም ባደረጉት ጥናት ሁለት ሦስተኛ አማቶች ምራቴ ታገለኛለች ማለታቸውን ደርሰውበታል።
  • ከአማቶቻቸው ጋር እንደ ማንኛውም ሰው ተዋውቀው ቢሆን ኖሮ (እውቂያችን በጋብቻ ባይሆን ኖሮ) ሊወዷቸው ይችሉ እንደነበር የተናገሩት ምራቶች ከመቶዎቹ መኻል ከ50 ያንሳሉ። ምራታቸውን እንደ ማንኛውም ሰው ተዋውቀዋት ቢሆን (ጋብቻ ባይዛመዱ ) ኖሮ ሊወዷት ይችሉ የነበሩት አማቶች ግን ከመቶዎቹ ውስጥ 71 ሆነው ተገኝተዋል።
  • አማታቸውን ለብቻቸው ፊት ለፊት ከሚያገኟቸው ወይም መስቲካ ጸጉራቸውን ከሚያጠባብቀው የትኛው እንደሚሻላቸው ከተጠየቁት ምራቶች መሐል 38% መስቲካ ጸጉራቸውን ቢያጠባብቀው እንደሚመርጡ ተናግረዋል። (ፍርሃታቸውን ያመለክታል)
  • ከተጠየቁት አማቶች ውስጥ 78% ምራታቸው ለልጃቸው ትክክለኛዋ ሚስት እንደሆነች ያስባሉ። ጣልቃ ባይገባባቸው ኖሮ 74 ከመቶ ምራቶች አማቶቻቸውን አሁን የሚጎበኟቸውን ያህል ወይም ከዚህም የበለጠ ቶሎ ቶሎ እንደነበር ገልጸዋል (ሊቀርቧቸው ማለት ይሆናል)።
የሴቶቹ ነገር

    ወንዶቹም ቢሆን አማት አላቸው። ይሁን እንጂ ውጥረቱ የሚታየው በአመዛኙ በባል እናት እና በሚስቱ መኸል ነው። ማለትም በምራትና በሴት አማቷ መኻል ነው። በአፐር ጥናት 163 ሰዎች “ከአማቴ ጋር ያለኝ ግጭት የረዥም ጊዜ መጨናነቅ አስከትሎብኛል ያሉ ምራቶች 60%’ ሲሆኑ “የሚስቴ እናት ራስ ምታት አስከትላብኛለች” የሚሉ ወንዶች 15% ብቻ መሆናቸው ይኸንኑ ያመለክታል።ይኼ ጉዳይ የወንዶች ሳይሆን ለምን የሴቶቹ ሆነ?

አንደኛ፡ በአማት ላይ ባሕላዊ ጣጣ፡- የሴት አማትን አጨልሞ የሚያሳየው ባሕል አንደኛው ምክንያት እንደሆነ የጉዳዩ ጠበብቶች ያሰምሩበታል ። ምራት ትዳር ውስጥ ስትገባ «ምራት ተጠቂ፣ አማት ግን አጥቂ- የአማት ምላስ ረዥም፣ ምራት ደግሞ የፈረደባት» እሚለው ባሕላዊ አስተሳሰብ በልቦናዋ ተቀርጾ ነው። (ይህ በአማቷ ለመቀየም ያገረገረች አድርጓት ነው ትዳር ውስጥ የምትገባው)።ይህ በሥጋት የተሞላ ልብ በአማቷ ፊት በሆነች ጊዜ እንድትደነባበር ያደርጋትና ስህተት ትሠራለች። ከድጡ ወደ ማጡ እንዲሉ የባሰ ለአማቷ ትችት ይዳርጋታል።

ሁለተኛ፡ የሴት ተንታኝነት፡-ለማንኛውም ግንኙነት እንደሚያደርጉት ከወንድ ይልቅ ሴት ስለ ግንኙነት በመተንተን እና ግንኙነትን ለማሻሻል በመጨነቅ ጊዜያዋን ታውለዋለች።አማት ሳታስበው የተናገረችው ፣ ወይም ማመስገን ሲገባት የረሳችው እና የመሳሰለው ምራትን ያሳስባታል፤ያስከፋታል።ፋታም አይሰጥ፣ ግንኙነታቸውን ወዲያውኑ እንደ በረዶ ያቀዘቅዘዋል። ውጥረት ያሰፍናል። “በመኻላቸው ግድግዳ ያቆማል”።በብዙዎቹ ዘንድ ፍጥጫ ላይም ያደርሳል። ( በተጨማሪ  ከታች ማሳያ 1ና 2ን ይመልከቱ)።
 ዲያና ብራን  እንደሚሉት ፣ወንድ ግን እንደዛ አይደለም። ጠብ ሲነሳ ቸል ይለዋል እንጂ መፍትሔ በመፈለግ ጉዳዩን ሲያብሰለስለው አይቆይም ። ቴሪ ኦበርክም ይኸንኑ ያጠናክራሉ።“ወንድ በሰላም መኖር ብቻ እንደሚበቃውና አማቱን የግድ ማፍቀር እንደማያስፈልገው ይረዳል”። አማቱን መውደድ የማይቻል ሲሆንበት እንኳ ያንን ሲያወጣና ሲያወርድ አይገኝም። ባብዛኛው ወንድ ለምን እንዳልተወደደ መረዳት አያስፈልገውም። ይህ ለምን አልሆነም ብሎ አይጠይቅምም። ሴት ግን ለምን እንደሆነ ማወቅ ይገዳታል። "ለምድነው አማቴ የማትወደኝ?" ፣ "ምራቴ በእኔ ላይ የምትቃወመው ነገር መኖሩ ለምንድነው?" የመሳሰለውን ታስባለች።

ሦስተኛ፡ ትዳሩ ሲመሠረት አማትም ምራትም ከጋብቻው በኋላ አንዳቸው ከሌላቸው እናገኘዋለን ብለው የሚጠብቁት ይኖራል። 
ሱዘን ኤበል ሊበርማን እንደሚያስረዱት ፣ የሁለቱም ወገኖች ምኞታቸው ከጋብቻ በፊት የተገለጠ አይሆንም። ከጋብቻ በኋላ ሲገለጥ ደግሞ የሚያገኙት ከጠበቁት ጋር የማይገጣጠም እንዳውም የሚላተም ሆኖ ያገኙታል።ተስፋውን ያላገኘችው ወገን ክህደት እንደተፈጸመባት ይሰማታል፣ ትበጠበጣላች።የጎደለባት ወገን ስለመበጥበጧ ተስፋውን ያጎደለችውን ወገን ትከሳለች፣ ትወቅሳለች። ታዝንባታለች።

አራተኛ 4፡ ያልተቆረጠ እትብት/ትስስር፡   አፕተር እንደሚሉት እናቶች ከልጆቻቸው ጋር የጠበቀና ያልተቆረጠ ትስስር አላቸው።ከዚህ ግንኙነት ለመላቀቅ እና በመኻል ሌላ ሰው ለማስገባት ለእናቶች የሚያም ነገር ነው። በወጣትነታቸው ሴቶች ልጆች ከእናቶቻቸው ጋር ብዙ ይጣላሉ። ይህ ድንበርን ለማበጀት የመደራደር ጥበብ ያስክናቸዋል። በዚህም ምክንያት የባል እናትን የአማትነት ሥፍራን ከማስያዝ ይልቅ የሚስት እናትን የአማትነት ሥፍራን ለማስያዝ ይቀላል። ኧሊ ስሏት ፊሸር ስለ እናት ይኸንን ይላሉ፦ወንዶች እስኪያገቡ የሚቀራረቡት እና በህይወታቸው ዋና ሴት አድርገው የሚያዩት እናታቸው ናት። በኋላ የመጣች ሚስት ይህን ሥፍራ ትወስደዋለች። ይህ መሆን እንደሚገባው ብታውቅም ከልጇ የመላቀቅን ምጥ ግን ለእናት አያቀልላትም።

    ለመሆኑ ሴቶቹ ለምን አይደጋገፉም? እንዴት የአማትና የምራት ጉዳይ ዛሬም ድረስ የሚነሳ ይሆናል? ዛሬ 1950 አይደለም። የሴቶችን እኩልነት በማረጋገጥ ብዙ ተጉዘናል። ብዙዎቹ የዛሪዎቹ አማቶች ትናንት ለሴት ተቆርቋሪ የነበሩ ሊሆኑ ይችላሉ። ምናልባትም ከአሥር ዐመታት በፊት ከለየላቸው የሴቶች ተሟጋቾች ጋር ባደባባይ ስሜታቸውን የገለጹ ሊሆኑ ይችላሉ። ታዲያ ዛሬ ምን ተለወጠ? ለምን አማት ለምራቷ አትቆምም? አማትና ምራት ሁለቱም ሴት ሆነው ሳለ እንዴት አንዳቸው ለሌላቸው ጥብቅና አይቆሙም? ሴት ለሴት መደጋገፍ ለምን አይኖርም?
 ስቴፈኒ ኩንስ  የሙያ መስክ መስፋፋት ለዚህ አስተዋጽኦ አለው ይላሉ።ለትዳር ጀማሪዎች የሙያ መስክ አማራጭ መስፋፋቱ አዲስ ዓይነት የአማትና ምራት ግጭት አምጥቷል። አማቶች ሁሉ ምራታቸውን የቤት እመቤት ሆነው የባሎቻቸውን እጅ ጠብቀው እንዲኖሩ አይጠብቋቸውም።ልጆቿ በእድሜ ጨቅላ በነበሩ ጊዜ እየሠራች ያሳደገች የትናንቷ እናት የዛሬዋ አማት፣ ምራት ቤቷ ብትቀመጥ በበጎ ዐይን አታያትም። ምራት እርሷ ወስዳ ከነበረው የተለየ ምርጫ በመከተሏ አማት ይህን በራሷ ምርጫ ላይ የተነጣጠረ አድርጋ ታየዋለች። የራሷን ምርጫ ትክክለኛነት ከሚከላከል የውስጥ ስሜት የተነሳ የተለየ ምርጫ በተከተለች ምራት ላይ ነቃፊ ትሆናለች ።

   ስቲፈኒ ኩንሲ ይቀጥላሉ። ዛሬ ዘመን ላይ የላቀች እንድትሆን በሴት ላይ ያለው ግፊትም ቢሆን ሴት ለሴት እንድትቆረቆር የሚረዳ አይደለም።የቱንም ያህል በወንድና በሴት መኻል የእኩልነት ጉዳይ ተሻሽሏል ቢባልም ሴቶች ሌሎች ሴቶችንም ሆነ ራሳቸውን ለመለካት የሚያስቀምጡት ከወንዶች ይልቅ ከፍ ያለ መለኪያ ነው። የዛሪዎቹ ምራቶች ”ቤታቸውን ማሳመር፣ልጆቹን ማሳደግና አንዳንድ ጊዜም ጠቀም ያለውን ገቢ ማስገባት ይጠበቅባቸዋል ።
  
 ሩት ኔምዞፍ እንዲህ ይላሉ። ታዲያ ምራቶች ትንሽም እንኳ የተፈረደባቸው (ቅሬታ ያሳዩዋቸው) ሲመስላቸው የሚቆጡ ይሆናሉ። የሴቶች እኩልነትን መቀበል ለበርካታ ምዕተ ዓመት የቆየን በምራትና በአማት መኻል በጎ ፈቃድ ማጣትን በአጭር ጊዜ መለወጥ አይችልም።

ለሰላም ዕድል ይሰጠው፡

    ከላይ እንደተጠቀሰው በአማት እና ምራት መኻል ውጥረቱ መነሻ አለው? ቁም ነገሩ ግን ይህ የሚረግብበት ስልት አለው ወይ ነው? መልሱ አዎ አለው ነው። በእርግጥ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ጊዜ መውሰዱ አይቀርም። የሰላሙን መንገድ ለመጀመር ምራትና አማት ራሳቸውን በሌላኛቸው ሥፍራ አድርገው ጉዳዩን ማየት ያስፈልጋቸዋል። "እኔ በእርሷ ቦታ ብሆን ኖሮ ምን ይሰማኝ ነበር? ምን አደርግ ነበር?" ብሎ ማሰብ ማለት ነው። ስሜታቸው በክፉ እንዲመልሱ ቢተናነቃቸውም እንኳ አስልተው (ሆን ብለው ራሳቸውን በመቆጣጠር ማለት ነው) በተለይም በአስቸጋሪው ሁኔታ ቀናነት እና ትህትና ያለበትን ነገር መናገር ነው። ከአንገት በላይ ወይም ለይስሙላ ያደረጉት እንደሆነ ቢሰማቸውም እንኳ ከአፋቸው ክፉ እንዳይወጣ መጠንቀቅ ይጠቅማል።

    አማትም ሆነች ምራት እነዚሁኑ የጠበብቱን ጥቆማዎች ሊጠቀሙበት ይችላሉ። መጠቀሙን ከጀመሩባት ደቂቃ አንስቶ የግንኙነት መሻሻልን ያገኙበታል።

ችግር 1፡ ድንበርን መግፋት (ዘዴ ለምራት)

    አማት ሆዬ የድንች ገንፎ ስትሠሪ በትከሻሽ ላይ አሾልቃ አየት ታደርግና በአሠራርሽ ላይ አስተያየት ትሰጣለች። “ስልባቦቱ የተገፈፈ ወተት ነው እንዴ የምትጠቀሚው? ስልባቦቱ ያልተገፈፈ ወተት ነበር ጥሩ ገንፎ የሚወጣው” ትላለች እንበል።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

  
ሲልቪያ ሚኩኪ-ኤኒያርት  እንደሚናገሩት ፦በዚህ ጊዜ በምግብ አሠራርሽ የተጎነተልሽ ፣ አቃቂር እንዳወጣችብሽ እንደሆነ ይሰማሽ ይሆናል። ብዙ አማቶች እንዲህ ዓይነቱን ሃሳብ የሚሰነዝሩት ምራታቸውን ለማሳዘን ወይም ለማበሳጨት ብለው አይደለም። እንደ ብዙዎቹ አማቶች በሕይወቷ ብዙ ልምድ ያካበተች ስለሆነ ያንን ለማካፈል በመፈለጓ ነው የተናገረችው።

ምን ታደርጊ፡

    በዚህን ጊዜ ከሁለት አንድ ነገርን ማድረግ ትችያለሽ። የተናገረችውን ሥራ ላይ ለማዋል በማሰብም ባይሆን ጥቆማውን አድምጪ/ምክሩን ስሚ። “ኧረ? እንደዛ ነው እንዴ? ሌላ ጊዜ እንዳልሽኝ መሞከር ሳይኖርብኝ አይቀርም። ለዛሬው ግን እንደማውቀው እሠራለሁ” ብለሽ ስልባቦቱ የተገፈፈበትን ወተት መጨመር ቀጥይ። (ሌላም ቢሆን እያደረግሽ ያለሽውን መቀጠል ነው ለማለት ነው።)
ወይም
ለሰከንድም ያህል ቢሆን ቆም ብለሽ አማትሽ የተናገረችው እውነትነት ያለው መሆን-አለመሆኑን መዝኚ። ምናልባት እርሷ የተናገረችው ዘዴ የተሻለ ሊሆን ይችላል።ይህንኑ ለአንድ ጊዜ ሞክሮ ማየት ነው። በዚህ ጊዜ ስለ ጠቅላላ ምግብ አሠራርሽ፣ ስለ ቤት አያያዝሽ ወይም ስለ ልጆች አስተዳደግሽ አልተናገረችም። የተናገረችው ከምግብ አሠራር ስለ አንዲቷ ብቻ ማለትም የድንች ገንፎ ለመሥራት ስልባቦት ያለውን ወተት ስለመጠቀም ነው። ነገሩን አካብደሽ (ለጥጠሽ) በማየት ራስሽንም አማትሽንም አታስቸግሪ ለማለት ነው። (ራስን መግዛት)

    የተሰጠው አስተያየት ግን በመሠረታዊ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ከሆነ ያለሽን አቋም ግልጽ ማድረግ ነው። ለምሳሌ ምክሩ ወይም እርምቱ በልጅ አስተዳደግሽ ላይ ከሆነ፣ በጉዳዩ የባለሙያዎቹን (የጠበብቶችን) ምክር በመጥቀስ (ለምሳሌ የልጄ ሐኪም ያንን አላለችኝም ማለት ይቻላል) ወይም የልጅ አስተዳደግ በየትውልዱ እንደሚቀያየር የታወቀ ነው” በማለት ምላሽሽን መስጠት ነው።አንቺም (አማቴ) ስሙን የጠቀስሽው ሐኪም ስመጥር ነው። እኔ ግን የምከተለው የአዲሷን ሐኪም የዶ/ር እከሊትን ምክር ነው።ዶ/ር እከሊት ደግሞ ከምትያቸው ሐኪም ጋር የምትስተካከል ነች። (እውነትን በፍቅር መናገር)

ችግር 2 ፡ ስሞታ ( ለአማት ዘዴ)

    ምራትሽ ትንሿንም ነገር ሁሉ ለልጅሽ ስሞታ ትናገራለች እንበል።በሹራቧ ወይም በእራት ጊዜ በአቀማመጧ ላይ የሰጠሽው አስተያየት ሁሉ ያስከፋታል። “ይቺ ልጅ ምን አድርጊ፣ ምን ሁኚ ነው የምትለኝ?” ትያለሽ። በምትናገሪው ሁሉ ታኮርፋለች። ምንም ነገር አያስደስታትም። ልጅሽ ደግሞ ይህንኑ ከሚስቱ ተቀብሎ እርሷ እንዳለች እንድታደርጊ ይነግርሽ ይሆናል። ይህ ይከብድብሻል።እርሷ የማትከፋበትን ምንም ነገር ማድረግ እንደማትችይ ሆኖ ይሰማሻል።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

    ምራትሽ በትልቁም በትንሹም የምታስቸግረው (ኩርፍ የምትለው) ምናልባት ጎሽታን/አድናቆትን ፈልጋ ይሆናል ይላሉ 
ኦርበክ ።አትናገረው እንጂ ካንቺ የምትፈልገው ነገር “ምንም እንከን አይወጣልሽም፣ ልጄን ስላገባሽ ዕድለኛ ነኝ” ማለትሽን ለማወቅ ይሆናል።

ምን ታደርጊ፡

    ስለዚህ የምትፈልገውን አድናቆት ስጪያት። አድናቆቱም የተድበሰበሰ ሳይሆን ግልጽ ይሁን። ለምሳሌ፡- ይህ ቤት እንዴት ያለ ግሩም ነው ከማለት ይልቅ አድናቆት ሲሰጠው የሚገባ ነገርን ነቅሰሽ በማውጣት ያንን በሐቅ ማድነቅ ነው። "የሳሎን አያያዝሽን እወደዋለሁ። እንዴት ዓይነት ቆንጆ ዓይን ነው ያለሽ! ጥሩ እናት ነሽ ወዘተርፈ" እንደ ማለት ነው። ይህ ሰላምን ለማምጣት ዓይነተኛ መፍትሔ ነው። ባለፈ ስለጠፋውም (ከነበረ) ጥፋት እርምጃ መውሰድም ያስፈልጋል። ጥፋቱን ማንሳት እና “ያንን ያልኩት ለክፋት አልነበረም። ግልጽ ባለመሆኔ ይቅርታ አድርጊልኝ” ብሎ እልባት መስጠት ይበጃል። አለበለዚያም የቀድሞውን እርግፍ አድርጋ ትታ ወደፊት ለመጓዝ ያስቸግራታል። በዛው ተቸክላ ትቀራለች።

ችግር 3፡ ገደቡን ያለፈ ጥያቄ፡( ጣልቃ ገብነት) (ለምራት ዘዴ)

አማትሽ ልጇን (ባልሽን) ሁል ጊዜ ቅዳሜ እየወጣን ወይም እኔጋ እየመጣህ ምሳ አብረን እንበላለን ብላ ባልሽን ቃል ልታስገባ ትሞክራለች እንበል።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

    
ሊበርመን የምራትን ችግር እንዲህ ያስቀምጡታል፦በዚህ ጊዜ ሰማይ ምድሩ ቢገለባበጥብሽ (ብው ቢልብሽ) እውነት አለሽ። ይህን የመሰለ ቋሚ ፕሮግራም መጠየቅ በትዳር ጣልቃ መግባት ነው። ተገቢም አይደለም ። እናት አሁንም የመጀመሪያውን ሥፍራ የያዝኩት እኔ ነኝ ማለቷ ነው። የመጨረሻ ዓይነት መጥፎ አማት የልጇን ትዳር የምታቃልል ናት። ፊሸርም ይጠይቃሉ፦ ምራቷን ሳይጨምር ልጇን ለብቻው ዘወትር ለማግኘት ማሰቧ ደግሞ ሌላ ምን ትርጉም ይሰጠዋል? ያንኑ ማለት አይደል?

ምን ታደርጊ

    ለሁለታችሁም የሚስማማ ዓይነት ፕሮግራም ምን እንደሆነ ከባልሽ ጋር ተነጋገሩ። ከሁለት አንዳችሁ (እንደ ጠቢባኑ አስተያየት ባልዬው መሆን ይገበዋል) አንገታችሁን ቀና አድርጋችሁ ስሜታችሁን በግልጽ እና በድፍረት መናገር አለባችሁ። ለምሳሌ፡ በፍቅር ነገር ግን በጥብቅ እንደዚህ ዓይነት ቋሚ ፕሮግራም መከተል የሚሆንልን አይደለም። የዚህን ሣምንት ማክሰኞ ማታ ግን ራትን አብረን ብንበላ ደስታውንም አንችልም ማለት ይቻላል። ለእናንተ በሚስማማ ሁኔታ ግብዣ ስታቀርቡ ሁኔታውን በራሳችሁ አስተዳደር ሥር አደረጋችሁት ማለት ነው።አልፎ አልፎ እናትና ልጅ (ሚስትን/ምራትን ) ሳይጨምር ተያይዘው ቢወጡ መልካም መሆኑ ግን አይዘንጋ። በሁሉም ወገን የሚወደድ ሆኖ የሚገኝበት ጊዜ አለ። የዛን ጊዜ በሁሉም ወገን የሚደነቅ ይሆናል

ችግር 4፡ ገመድ ጉተታ፡ ( ለአማት ዘዴ)

    ልጅሽን የኮምፕዩተር ማተሚያሽን መጥቶ እንዲጠግንልሽ ፈለግሽና ይህንኑ ነገርሽው እንበል። እርሱ ግን ሚስቴ አይሆንም ብላለች ይልሻል።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

   እንደ 
ኔምዞፍ አባባል ምራትሽ በልጅሽ ጭንቅላት ከርቀት መቆጣጠሪያ ያላስገባች (ያልተከለች) መሆኑን አስታውሺ። ልጅሽ አንቺን ለመርዳት ወይም ለመጎብኘት ወይም ካንቺ ጋር በስልክ ለማውራት ጊዜ የለኝም ቢል ኃላፊነቱ የእርሱ እንጂ የምራትሽ አይደለም። ፊሸርም ያስፋፉታል። ምናልባት ይህን ሲል ሚስቱንና ልጆቹን ካንቺ ማስቀደሙ ይሆናል። ይህንኑ ላንቺ ለመናገር ግን ፈርቶ ይሆናል። ስለዚህ ነው በሚስቱ ያሳበበው። እርሷን ኅላፊነት ወሳጅ (የጭዳ ዶሮ) አድርጓት ይሆናል ለማለት ነው።
 ልጅሽን ለሰው አሳቢና ሰውን አፍቃሪ አድርገሽ አሳድገሽ ከሆነ አሁን ሚስቱን የመጀመሪያ (ከሁሉም በፊት ማድረጉ) ለዚህ ነው  ይላሉ ሊበርማን በእርግጥ ምራት በልጅሽ ላይ ብዙ ጉልበት እንዳላት ማለትም ተሰሚነት እንዳላት የታወቀ ነው። አንቺን ለማግለል (ለማቆራረጥ) ትሞክራለች ቢባል የማይመስል ነገር አይደለም። የሚመስል ነገር ነው ። ይኸን የሚሉት ደግሞ ብራን ናቸው

ምን ታደርጊ፡ 
     ይህን ስለማድረጓ ጥርጣሪ/ግምት ካለሽ ማድረግ የሚገባሽ መልሶ ማጥቃት አይደለም። ይልቁንም በተቻለ ሁሉ በጎ ፈቃድን ማሳየት ነው፡፡ ምራት ብዙውን ጊዜ ባለፈ ህይወቷ (በሌሎች) ስለደረሳባት ጉዳት አማትን ልትበቀል ትችላለች።አማትን ልታገልል (ፊት ልትነሳ) ትችላለች። የሚሻለው ከእርሷ ጋር ለመወዳጀት መሞከሩ ነው።

    ምሳ ጋብዢያት። ወይም ወሬን ለማውራት (ለመጨዋወት) ያህል ደውይላት። ለጊዜው ካንቺ ጋር ያለውን ግንኙነት መቀጠል (መጠገን ) አስፈላጊ አድርጋ አትቆጥረው ይሆናል። ይሁን እንጂ የመጀመሪያውን እርምጃ (ምናልባትም የመጀመሪያዎቹን አምስት እርምጃዎች ) ባንቺ በኩል ከወሰድሽ እንደዛ ማሰቧ ሊለወጥ ይችላል።ከልጅሽ እርዳታን የምትጠይቂበትን ዘዴ፣ ወይም ምክር የምትሰጭበትን ዘዴ፣ ወይም ከእርሱ ጋር የመገናኘት ዘዴን መደራደር ያሻል። 

ከጀርባ ምራትን መውጋት፡ ( ለምራት ዘዴ)

    ለምሳሌ፡ አማትሽ ለባልሽ "ሚስትህ ብዙ ትሠራለች" ብላ ስሞታ ልትናገር ትችላለች።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

    ይህን የተናገረችው ልጇ የሚገባውን እንክብካቤ አለማግኘቱ አሳስቧት ነው። 
ሲልቪያ ሚኩኪ-ኤኒያርት እንደሚሉት እናቶች ብዙ ጊዜ ልጆቻቸው ካገቡ በኋላም ስለእነርሱ የሚገዳቸውን መሆኑን ይናገራሉ ።ደስተኛ ነው ወይ? ጥሩ እንክብካቤ እያገኘ ነው ወይ? ከላይ ተጠቅሶ እንደነበረው እናቶች በመርህ ደረጃ ወንዶችና ሴቶች እኩል ናቸው ብለው (በሴቶች እኩልነት) የሚያምኑ ሊሆኑ ይችላሉ። እንደዛም ሆኖ ምራታቸው ልጃቸውን ከሁሉም በፊት እንዲያስቡት/እንዲንከባከቡት ይፈልጋሉ። አፕተር ምክንያቱን ሲያስቀምጡ፡-"ወንድም ቢሆን ልጃቸው ነው"ና።

ምን ታደርጊ፡

    ለዚህ ባልሽ ዘዴ ሊያበጅለት ያስፈልጋል። በዚህ በኩል እናቱ የምትለውን ባለማዳመጥ ቀዳዳውን መዝጋት ያለበት ባልሽ ነው። ነገሩ ባንቺና በእርሱ መሐል ማለቅ ያለበት ጉዳይ ነው። ሊሰንም (Allison)  ይመክራሉ። ሲያናግራት እንደዚህ ሊል ይችላል። “አየሽ እናቴ እወድሻለሁ። በሌላ በማናቸውም ጉዳይ ልንነጋገር እንችላለን። ስለሚስቴ ግን ካንቺ ጋር በጭራሽ አልነጋገርም"።

የምትፈልጊውን መከልከል (ለአማት ዘዴ)

ለምሳሌ ምራትሽ ከልጆቿ ጋር (ከልጅ ልጆችሽ ) ጋር ቅዳሜን አብረሻቸው ለማሳለፍ ፈልገሽ ከአንቺ ጋር እንዳይውሉ ልትከለክል ትችላለች።

ነገሩን እንደዚህ ተመልከቺው

    በተለይም ያለምንም መነሻ (ማብራሪያ) ልጆቹን ለመንከባከብ ስትጠይቂያት (ዕድል ስትሰጪያት) መከልከልሽ ሊጎዳ መቻሉ እውነትነት አለው። ነገር ግን ይህን ለማስታወስ ሞክሪ። ምራትሽ ለውሳኔዋ ምክንያት አላት። ከምክንያቶቿ መኻል አንዱ ሊሆን የሚችለው ያንቺ ደምብ አይመቻት ወይም እስከነጭራሽኑ ሥርዓት የማስያዝ ደምብ የለሽ (ሲበዛ ታሞላቅቂ) ይሆናል። ወይም ለራሷም ቢሆን ከልጆቿ ጋር ልትሆን የምትችልበት ሌላ ጊዜ ስለሌላት ያቺኑ ቆርሳ ለማካፈል እያሳሳት ይሆናል።

ምን ታደርጊ፡
ብራን መፍትሔውን ያሰማሉ።በቤትሽ ቴሌቪዥን 24/7 የማይዘጋ ከሆነ ያንን መዝጋት ነው። ቸኮላትና ኬክ ከፍሪጅሽ አይጠፋ ይሆናል።ያንንም ማጥፋት ያስፈልግ ይሆናል። ልጆቹን ልውሰድ ብቻ ሳይሆን ምን ደምብም ሥራ ላይ እንዲውል እንደምትፈልግ ምራትሽን አብረሽ ጠይቂ። ከዚያ ይህንኑ አድርጊው። ልጆቹ በተወሰነ ሰዓት የሚተኙ ከሆነ እንደዚህ መደረጉን አረጋግጪ ። “ያንቺ ልጆች አይደሉም”። ምራትሽ ሙሉውን ቅዳሜ ልትሰጥሽ ባትፈልግ ወይም ባትችል የተሻለ ቀዳዳ (ቀን ) መቼ ሊገኝ እንደሚችል ጠይቂ። ለምሳሌ ልጅሽና  (ባልሽና) እርሷ ለብቻቸው ለመሆን ባቀዱበት ምሽት ሊሆን ይችላል። ንግግሩን ስትጀምሪ ልጆቹን ልውሰድ ሳይሆን፣ በምን ልረዳሽ እችላለሁ? ልጆቹን ብጠብቅልሽ/ብወስድልሽ ይረዳሻል ወይ በማለት ይሁን? ልጆቹን ለመውሰድ መብትሽ እንደሆነ አታስቢ። ምራት እርዳታውን አትፈልግም ማለት አይደለም። በምን ልርዳሽ? ይህን ባደርግልሽ ይሆናል ወይ? ብሎ መጠየቅና እርዳታውን የማትቀበል ሲሆን (እምቢ ስትልም) አለመከፋት ነው።

እነዚህ ለማሳያነት ተነሱ እንጂ በዚህ ርዕስ ሊጠቃለሉ የሚችሉ ብዙ ጉዳዪች አሉ። ለሁሉ ነገር እጋበዛለሁ ብለሽ አትጠብቂ። ወደ ሆስፒታል መዋለጃ ክፍል፣ ለሽርሽር፣ ለሁሉ ድግስ፣ ምራትሽ ለምታደርገው ልዩ ልዩ ዝግጅት/ድግስ ሁሉ እንድትጠሪ/እንድትጋበዢ አትጠብቂ።

    ለማጠቃለያ እንዲሆን አምስት እጅግ ውጤታማ የሆኑ የአማት ልማዶችን እና ሰባት እጅግ ውጤታማ የሆኑ የአማት ልማዶች የተባሉት ከታች ተሰጥተዋል።

አምስቱ እጅግ ውጤታማ የሆኑ የአማት ልማዶች

1. በቤተሰብ ደስታ እንዲሁም ቀልድ ምራትን ማሳተፍ

  
ሲልቪያ ሚኩኪ-ኤኒያርት ይጠይቃሉ።  ልጅሽ እና ሚስቱ አንቺን አስቀምጠው ከት ብለው ቢስቁ ምን ይሰማሻል? “አሁን ምን ያስቃቸዋል?” በማለት አለመደሰትሽን መግለጥሽ እንደማይቀር የታወቀ ነው። ታዲያ እንደራስ ማየት ነው። እንደሚሉት ቤተሰብ አብሮ በሚሆንበትና ፈንጠዝኛ በሚያደርግበት ሁሉ ምራትሽ እኩል ተካፋይ እና ተዋናይ እንድትሆን ማድረገ ተገቢ ነው። ቤተዘመዱ ሁሉ ለገና የሆነ ዐይነት ቀለም ቢጃማ የሚለብስ ቢሆን ለእርሷም ያንኑ ዐይነት ቢጃማ ስጦታ መስጠት ነው ።እስከ መፈጠሯም መርሳት ፣ ከሌሎች ለይቶ ስጦታ ለእርሷ አለመስጠት ወይም ተገቢ ያልሆነ ስጦታ መስጠት ፣ አለማመስገን እና አለማድነቅ ወዘተርፈ ከቤተሰቡ ማግለል ነው፡፡ ይህ ደግሞ ምራትን የሚጎዳ ነው። አንድ በWestern Journal of communication) የወጣ ጥናት እንደሚያመለክተው በቤተሰብ ደስታና ፈንጠዝኛ እንዲሳተፉ የተደረጉ ምራቶች በአስቸጋሪ ሁኔታ ሳይቀር ከአማቶቻቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለመጠበቅ ፈቃደኝነታቸው እንደሚጨምር ያመለክታል።

2. ሁል ጊዜ እንደተማሪ አትቁጠሪያት/ እንደ እኩያ እዪአት

ሁሉን አውቃለሁ የሚልን ማን ይወዳል?አማት ሁል ጊዜ ለመምከር እና ለማስተማር የበቃች እና ምራት ግን ሁል ጊዜ የምትመከር እና የምትነገር ተማሪ አድርጋ ካየች ምራትን ይጎዳል።ዲያን ብራን እንደሚመክሩት ከሆነ   ባንዳንድ ጉዳዮች አዋቂም ምራትዬዋ ትሁንበት። አማት ሁሉን ነገር እኔ አውቃለሁ አትበል። ምራታችሁ የተሻለ የምታውቀው ነገር ካለ ያንን እንድታስረዳ መጠየቅ ነው ። ለምሳሌ የአትክልት ሥራ፣ በኦን ላየን ዕቃ መግዛት፣ዮጋ የመሳሰለውን

3. አስቀድሞ ማስታወቅ፡ 
ደስ ባለሽ ጊዜ ሁሉ  በቤቷ ዘው አትበይ። "ጎራ ለማለት አሁን ጥሩ ሰዓት ነው እንዴ?" ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው። መልሱ አይደለም ከሆነም ይህንኑ በደስታ መቀበል ያሻል። የምራትሽ ቤት ቁልፍ ቢኖርሽም ቤቱን ከፍተሽ እንድትገቢ ካልተጠየሽ ወይም አስቸኳይ ጉዳይ ገጥሞ ካልሆነ በስተቀር አትጠቀሚበት።

4. አስፈቅጂ። 
ምራት እና ልጅሽ የጎላ ስህተት ሊሠሩ ሲሉ ‘ከስህተት የሚያተርፍ’ አስተያየትሽን መስጠት ያስፈልግሽ ይሆናል። ሱዘን ኤበል  ይሁን እንጂ ይላሉ።ይሁን እንጂ  አስተያየትሽን ለማካፈል ይፈቀዱልሽ እንደሆነ ፈቃድ መጠየቅ ነው። አዎ ካሉ (ፈቃዱን ከሰጡሽ) ለዛን ጊዜ ብቻ ሃሳብሽን ለማካፈል መብት አለሽ። ይህ ፈቃድ ለሌላ ጊዜ የሚያገለግል አይደለም።

5. ያለፈውን መተው ፡
ምራታችሁ በሠርጓ ዕለት አብዝታው ፥ በጥብጣችሁ ይሆናል። ያ ግን ያን ለት የሆነ ነው። አልፏል። ዛሬ ሌላ ቀን ነው።መተው ነው ። የሩት ኔምዞፍ ምክር ነው።

ሰባቱ እጅግ ውጤታማ የምራት ልማዶች*

1. አማትን ማስታወስ ፡ 

አማቶች ብዙ ጊዜ ድንበር ላለመግፋት ይጠነቀቃሉ። በዚህ መኻል እንዳይዘነጉ ወይም እንዳይረሱ ይሠጋሉ። ምራቶች ይህን በመረዳት ሕይወታቸውን ለአማት ማካፈል፣ እንዳልተረሱና እንደተከበሩ፣ በቤተሰቡም እንደተካተቱ ማረጋገጫ መስጠት ነው። ለምሳሌ ፎቶ እና ሌሎችንም መረጃዎች ከመጠየቃቸው በፊት እና በቶሎ አብዝቶ መላክ። ድምበር እንዳይገፋም ያረጋጋቸዋል።

2. ለአስተያየት ጆሮ አለመስጠት፡ 

በቀላሉ አትከፊ። ሁለተኛው ልጅ እንደወለዳችሁ አማት “እውነት አሁን ሥራ ልትመለሺ ነው?” ይሉሻል እንበል። ታዲያ የሆነስ እንደሆነ? ነገሩን ንቆ ወይም ስቆ ማሳለፍ ነው። ሌላ ምን ያስፈልጋል? ቀድሞውኑ አማት አቃቂር ታወጣለች ብለው ስለሚያስቡ በትንሹ ነገር ምራቶች ሊቆጡ ይችላሉ። ይሁን እንጂ አንዳንዱ ነገር አንቺን ለማጥቃት እንደተሰነዘረ ማሰብ አይገባም። አማቶች ስለ ቤቱ፣ ስለልጆቹ ጠባይ አስተያየት ሊሰጡ ይችላሉ። ሰምቶ እንዳልሰማ መተው ነው።

3. ብስጭትን ወዲያው መግለጽ፡ 

መስመር የለቀቀ ነገር አማት ስትናገር/ስታደርግ ወዲያው በጉዳዩ ተበሳጭቻለሁ ብሎ መናገር እና ድንበርን ማስመር ነው። ነገርን ማሳደር “አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ” ነው። ማሳደር አያስፈልግም። ዝም ብሎ ማሳለፍ በኋላ ትልቅ ቁጣ ሆኖ ይፈነዳል። ለምሳሌ አብዝተው ጣልቃ የሚገቡ ከሆነ፣ ወይም አብዝተው ምክር የሚሰጡ ከሆነ፣ እግር ወደ ቤትሽ የሚያበዙ ከሆነ ከባል ጋር ተመካክሮ በእንጭጩ ድንበርን ማስመር ይሻላል።

4. መከበር፡ 
ከኋላ ወንበር መቀመጥ፡አማቶች ሁሉ መከበር ይሻሉ። ለምሳሌ የፊት ለፊቱን የመኪና መቀመጫ መልቀቅ (ሊያውም እምቢ ለምትለው ነገር)። (ለእኛ ማህበረሰብ ባሕላዊ አከባበር እንዳለ ይታወቃል። ለምሳሌ መቀመጫን መልቀቅ፣ ከተቀመጡበት ተነስቶ መቀበል ወዘተርፈ ሊተካው ይችል ይሆን?)

5. እርዳታ/ ምክር መጠየቅ፡
 ትልቅ ነገርን እንዲያደርጉ መጠየቅ (መመልመል) ያስፈልጋል። ለምሳሌ ለባልሽ ልደት ኬክ እንዲጋግሩ የተፎካካሪነት መንፈስን ወደ ትብብር መንፈስ መቀየር ነው። አስቀድመውንም ለመስጠት የሚፈልጉት ስለሆነ ሲጠየቁ ደስ ይሰኛሉ።

6. መሸሸግ፡ 
የአማት ጠባይ ሰውን ሁሉ የሚበጠብጥ ከሆነ አንዳንዴ መሸሸጉ ይበጃል። ስለዚሁ ባል እናቱን እንዲያናግር ማድረግ ነው። በማናገሩ የምትጎዳ ቢሆን እርሱን ፈጥና ይቅር ልትል ትችላለችና።

7. በዓልን አብሮ ማክበር፡
 ብዙውን ማህበራዊ ግንኙነት አንቺ ታደርጊውና ቤተሰብሽ (ወላጆችሽ) አንድ ላይ መሰባሰቡን ትመርጪ ይሆናል። ይሁን እንጂ የባልሽ ወላጆች በብቃት የሚካፈሉበትን ሥርዓት መክፈት (ለምሳሌ የምሥጋና ቀን ድግስን በማዘጋጀት) ከአማትሽ የምስጋና ያዥጎደጉድልሻል።

ጨረስሁ!


ያገኘሁትን አካፈልኳችሁ። አልሰሰትኩም።ስላነበባችሁልኝ እግዚአብሔር ይስጣችሁ


ጠበብቱን ተዋወቋቸው፡

ቴሪ አፕተር Terri Apter, PhD.,for her 2009 book What Do You Want From Me? Learning to Get Along With In-Laws.

ማሳያ ፩፡

ከጫጉላ ሽርሽር ስመለስ አማቴ ዕቃችንን ሁሉ ፈትታ፤ ዱቄትና ስኳሩን በየዕቃው ገልብጣ፣ ሌላውንም ዕቃ ሁሉ ሥፍራ ሥፍራውን አስይዛ ፣ የአበባ እቅፍ በመሐል ጠረጴዛው ላይ አኑራ ቤቴን በደንብ አሳምራ ጠበቀችኝ። እርዳታ በሚል ስም ያደረገችውን ይህንን አስታውሳለሁ። ምስጋና ቢስ እንዳልባል ምንም አልተናገርኩም። ነገር ግን በመሪር ብስጭት ነበር የተበሳጨሁት። የራሴን አዲስ ቤት እኔው በወደድኩት መንገድ ላስተካክለው የነበረኝን ዕድል ሰረቀችብኝ/አጨናጎለችብኝ። ሥራ በነበርንበት በሌላ አንድ ቀን ደግሞ ልብሳችንን ሁሉ ላውንደሪ አድርጋ ቤቱንም አስተካክላ ጠበቀችን። ይህን በማድረጓ ተቃወምኳት። እርሷም ኮስተር ብላ ረዳሁሽ እንጂ ምን አጠፋሁ? ደግሞም ነገሮች ተስተካክለው ሲቆዩት ልጄን ደስ እንዲለው ስለማውቅ ነው አለችኝ።


ማሳያ ፪፡

“ሐምራዊ ልብሴን ስለብስ ጥቁሩን ብለብስ ቀጭን /ሸንቃጣ እንደሚያደርገኝ ትነግረኛለች።ልጄን ሹራብ ያለበስኩት ጊዜ ለብርዱ ጃኬቱን ማልበስ ጥሩ ነው ትለኛለች። ምግብን በቅቤ የሠራሁ እንደሆነ ስለ ኮሌስትሮል አንስታ ትዘበዝብብኛለች።የአማቴን ድምጽ የማልሰማበት ሥፍራ የት በደረስኩ?”


ዲያና ብራን Deanna Brann , Ph.D ., the author of Reluctantly Related:Secrets of Getting Along with Your Mother -in-Law or Daughter -in-Law.


ቴሪ ኦርበክ Terri Orbuch, PhD., a professor of sociology at Oakland University , in Rochester , Michigan, the author of 5 simple steps to take your Marriage from Good to Great

ሱዘን ኤበል ሊበርመን Life coach Susan Abel Lieberman,D.,the author of The Mother in law’s Manual

ኧሊ ስሏት ፊሸር Ellie Slott Fisher, a relationship expert and the author of It’s Either Her or Her. A Guide toHelp a Mom and Her Daughter-in-Law get Along

ስቴፈኒ ኩንስ Stephanie Coontz , a professor of history and family studies at Evergreen State College, in Olympia , Washington, and the author of A strange Stirring: The Feminine Mystique and American Women at the Dawn of the 1960s

ሩት ኔምዞፍ Ruth Nemzoff, Ed.D.,a resident scholar in Women’s studies at Brandeis University, in Waltham, Massachusetts, and the author of Don’t Roll your Eyes: Making In-Laws Into family

ሲልቪያ ሚኩኪ-ኤኒያርት Sylvia Mikucki-Enyart , Ph.D., an assistant professor of interpersonal communication at the University of Wisconsin -Stevens Point who has studied the mother-in-law /daughter -in-law relationship


ፊሸር (Fisher) ማንነታቸው አልተገለጠም 
አሊሰን (Allison) ማንነታቸው አልተገለጠም




Comments

Popular posts from this blog

Comparative Theology የነገረ መለኮት ንጽጽር (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት)/ በብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ሲኖዳ ሳልሳዊ

 የነገረ መለኮት ንጽጽር  (በኦርቶዶክስና በፕሮቴስታንት): የወደደ  ሁሉ በነጻ እንዲጠቀምበት ተፖስቷል። ይሁን እንጂ መብቱ በሕግ የተጠበቀ ስለሆነ በየትኛውም መልኩ ለንግድ እንዲውል አልተፈቀድም። ልዩ ልዩ መግቢያ የሚለውን መጀመሪያ ካነበቡ በኋላ የተቀረውን በተመረጠው ቅደም ተከተል ማንበብ ይቻላል። ልዩ ልዩ መግቢያ   ጥምቀት   ትውፊት (ወግና ልማድ)   መካከለኝነት   ጾም የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ መንፈሳዊ ስጦታዎችና በልሳኖች የመናገር ስጦታ   ሥርዐት ንስሐ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ

የድንግል ማርያም ክብሯና ዘላለማዊ ድንግልናዋ (1)  ድንግል ማርያምን ስለማክበር (2) ለጥያቄዎች መልስ (ሀ) ድንግሊትን ‘የወይን ግንድ (ተክል)’ና የ ‘ሕይወት በር’ የሚል ማዕረግ  ለምን እንሰጣታለን? (ለ) ወደ ድንግል ማርያም መጸለይ ትክክል ነው ወይ? (3) የድንግል ማርያም ድንግልና ዘላለማዊነት (4) ለተቃራኒ አስተያየቶች መልስ (ሀ) “የመጀመሪያ ልጇን” የሚለው ሐረግ (ለ) “ሚስትህ” የሚለው ሐረግ (ሐ) “አብረው ከመሆናቸው በፊት ጸንሳ ተገኘች” (መ) “የመጀመሪያ ልጇን እስክትወልድ አላወቃትም” (ሠ)  “ወንድሞቹ” የሚለው ሐረግ   የቅድስት ድንግል ማርያም  ክብሯ (1) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ድንግል እመቤታችንን አያከብሩም፤ ደግሞም እንድታማልድላቸውም (እንድትማልድላቸውም)  አይጠይቋትም።ከእነርሱ ወገኖች አንዳንዶቹ እንዲያውም ጫጩቱ ከተፈለፈለ በኋላ ዋጋ ከሌለው የዶሮ እንቁላል ቅርፊት ጋር እስከሚያመሳስሏት ይደርሳሉ።ይህ የተጋነነ ማቃለል የመጣው ምናልባት ሮሜዋውያን ካቶሊኮች የተጋነነ ማክበር ስለሚያከብሯት ለዛ ተቃርኖ ከማሳየት አዝማሚያ ሊሆን ይችላል። ስለዚህም ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን አንዱንም የእርሷን በዓል አያከብሩም።  (2) አንዳንዶቹ የፕሮቴስታንት ወገኖች ድንግል ማርያምን “እህታችን” ይሏታል። (3) በተጨማሪ አንዳንዶቹ ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ጌታ ኢየሱስን በድንግልና ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር ጋብቻዋን ፈጽማለች፤ የ‘ኢየሱስ ወንድሞች’  ወይም የ’ጌታ ወንድሞች’ ተብለው የተጠሩ ልጆችን ወልዳለች ይላሉ።  (4) ፕሮቴስታንት ወንድሞቻችን ቤተክርስቲያናችን ለድንግል እመቤታችን የሰጠቻቸውን አንዳንድ የማዕረግ ስሞችም ይቃወማሉ።  (5) ድንግልን ያለማክበራቸው አንዱ...

ስለ "አስታዋሽ ጾምና በዐሉ" ጥያቄና መልስ

 ስለ "አስታዋሽ ጾምና በዐሉ" ጥያቄና መልስ  ለዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ፦ ሕልውናችንን-ነጻነትችንን የማረጋገጥና የማስቀጠል አንድነታችንን የመጠበቅና የማጠንከር  በእሴቶቻችን የመደሰት፣ እነርሱን የመንከባከብና የማስተዋወቅ  በረከታችንን የማብዛትና የማካፈል  ኃላፊነቶቻችንን በማኅበር ፣ በማስተዋልና በትጋት እንድንወጣ “ጾሙና በዐሉ" አስታዋሽ ባሕላዊ ምልክታችን ይሁንልን   ጥያቄ 1 ፡ አድማጭ ተመልካቾቻችን እንኳን ደህና መጣችሁ።የከበረ ሰላምታችን ይድረሳችሁ። ዛሬ የምንወያየው ከአቶ ባንቱ ገብረማርያም ጋር ይሆናል። አቶ ባንቱ በሙያው ፋርማሲት ነው። እንደነገረኝ በእምነቱ ደግሞ ባፕቲስት ነው።ለዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ ባሕላዊ ምልክት የሚሆን “ጾምና በዐልን” በማስተዋወቅ ላይ ይገኛል። የምንወያየውም ስለዚሁ "ጾሙና በዐሉ" ምልክትነት ይሆናል።  አቶ ባንቱ ለመወያየት  ወደ እኛ በመምጣትህ አመሰግንሃለሁ። እንኳን ደህና መጣህ። አንተ እያልኩ ልቀጥል ወይስ አንቱ? መልስ 1፡ ዎገኔ፡   እንኳን ደህና ቆየኸኝ። ለአድማጭ ተመልካቾቻችሁም ሰላምታዬ ይድረስልኝ። አንተ በለኝ። የሚያውቀኝ ሁሉ አንተ ነው የሚለኝ።  ጥያቄ 2 ፡ እሺ  አንተ እያልኩ እቀጥላለሁ። አቶ ባንቱ፣ ምናልባትም ብዙ ሰው ስለማያውቅህ  እስቲ ስለራስህ በአጭሩ ንገረን። ወዲያውም መክፈቻ ይሆነናል መልስ 2 ዎገኔ ፦ አስቀድሜ ይኸን ዕድል ስለሰጠኸኝ ላመሰግንህ እወዳለሁ። አድማጭ ተመልካቾችህንም ጊዜ ወስደው  ውይይቱን  ስለሚከታተሉ ላመሰግናቸው እወዳለሁ።አዎን፣ ባንቱ ገብረማርያም እባላለሁ።እንደነገሩኝ የተወለድኩት ሽርካ በዛሬ አጠራሩ በአርሲ ዞን ነው።ነፍስ ያወቅሁትና ትምህርት ...