ፋኖ ያሸንፍ!
ባለፈው ጊዜ “ፋኖ እንዲያሸንፍ ለምን እንደምመኝ /እንደምፈልግ ጊዜ ካገኘሁ እጽፍበታለሁ ፤ እስከዚያው ግን ምኞቴ እንዲደርስ መርቁኝ “ ብዬአችሁ ነበር።
በአጭሩ፦ፋኖ እንዲያሸንፍ መመኘቴ “አንቺም ትሞቺብኝ ይሆን ወይ? (እንደ ተረቱ)” በሚባል አስተዳደር ላይ የተጠረቀመውን መዝጊያ ወለል አድርጎ ይከፍታል” በሚል እሳቤ ነው። ("አንቺም ትሞችብኝ ይሆን ወይ" ማለት እንዲወድቅ የማይፈለግ ቅን መንግሥት ለማለት ነው። ተረቱን ለማወቅ የሚፈልግ በአስተያየት መስጪያ ላይ ይጠይቅ)
እንደሚታወቀው የዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ ከበዳዮቹና ከአስጨናቂዎቹ ይታደጉት ዘንድ በቅርቦቹ አሥርት ዐመታት በኢትዮጵያ ለተነሱት መንግሥታት አቤቱታውን ሲያሰማቸው ኖሯል። ሰላማዊ በተባለ መንገድ ጥያቄውን አቅርቦላቸዋል። ይሁን እንጂ ሊከላከልለት የፈቀደ የመንግሥት አካል ብቅ አላለም። በችግሩ አላዘኑለትም። ያም ቀርቶ መሳለቂያ ባላደረጉት ምንኛ መልካም በሆነ ነበር። እንዳውም አሁን በመጨረሻ በብዙ ሥጋት ውስጥ እያለ መንግሥት ራሱ “ወርሰህ ታጠቅ” ያለውን ጠመንጃ አስረክብ ብሎ ተነሳበት። ሌሎቹ ሳይነኩ ልዩ ኅይሉንም አፈረሰበት።ጦርም አዘመተበት።የዐማራ ሕዝብ ምን ምርጫ ነበረው? ምን ቀረው? የመከላከል ጦርነት ውስጥ ገባ። ለተጋድሎው ፋኖ ዐይነተኛ መሪው ሆኖ ብቅ አለ።እግዚአብሔር የዐማራን ሕዝብና ዎገኖቹን ሊያስበው መጀመሩ ነው መሰለኝ ሁኔታዎች ተገጣጠሙና ፋኖ የዐማራን ሕዝብና ዎገኖቹን የሚወጉትን ኃይላት የሚገዳደር ኅይል ሆኖ ወጣ።ታዲያ በዚህ እራስን የማዳን ጦርነቱ ነው ፋኖ እንዲያሸንፍ የፈለግሁት/የተመኘሁት።የአብርሃም አምላክና አምላክህ ይርዳህ ! ድሉን ይስጥህ ብዬዋለሁ።
ተሳስቼ ሊሆን ይችላል። ስለጦርነቱ ያለኝ አስተያየት ይኸው ነው።ለመታረም ግን ዝግጁ ነኝ። (ዐማራን የሚወጉት ኃይላት የሚሰጡትን ምክንያት ያልሰማሁ አይደለሁም)።
ከዚህ ከተጋድሎው ፍትሐዊነቱ ባሻገር ፋኖ እንዲያሸንፍ የምሻበትን ሌሎች ምክንያቶች ከዚህ በታች እዘረዝራለሁ።
1. ጦርነቱ በፋኖ አሸናፊነት ከተደመደመ በዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ ላይ የሚፈጸመው የግፍ ሥራ ያቆማል (ቀዳሚው ይህ ነው)።
2. የሁላችንም አባቶችና እናቶች የጋራ መሥዋዕትነት ከፍለውና በትጋት ሠርተው ለጋራ ያወረሱንን አገር/መሬት ይኸኛው አካባቢ የእኔ ነው፣ ያኛው የአንተ አይደለም ሳይባባሉ ልጆቻችን በጋራና በእኩል መብትና ግዴታ ሊኖሩባት ፥ ሊባረኩባት የምትችል አገር የማግኘት ዕድል ይቀርብላቸዋል።
3.ወላጆች (ከተለያዩ ነገዶች የሆኑ) በትዳር የወለዷቸው ልጆችና የልጅ ልጆች ያለውዴታቸው የአባታቸውን ወይም የእናታቸውን ነገድ ከመምረጥ እንዲላቀቁና ከአንድ ዐይነት ነገድ ከተወለዱ ልጆች እኩል መብታቸውና ግዴታቸው እንዲከበር መንገድ ይጠርጋል።
4.የአንደኛውን ወይም የሁለቱንም ወላጆቻቸውን ነገድ የማያውቁ (ከተደፈሩ እናቶች ወይም ከወሲብ ሠራተኞች በመወለዳቸው፥ ወይም ነገዳቸውን ሳያውቁ ወላጆች ስለሞቱባቸው ወዘተርፈ) ከተቀሩት እኩል መብታቸውና ግዴታቸው እንዲከበር ዕድሎች ይገኛሉ
በቁጥር 2፣3፥4 መብት ሲባል ለምሳሌ፦
- በግልም፥ በማኅበርም ያለ ሥጋትና ያለአድልኦ ከቦታ ቦታ መዘዋወር፣ መሥራት ፣መኖርም መቻል
- ሐብትና ንብረት ያለ ተገቢው ካሳ ወይም ተመጣጣኝ ምትክ በጉልበት አለመቀማት
- የመንግሥት ሥራን ወይም አገልግሎትን ለማግኘት የዘር ወይም የሃይማኖት እድልኦ/ ልዩነት እለመደረግ።
- ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን በረከት ለመሆን ለሁሉም እኩል ዕድል ማግኘት
ወዘተርፈ ለማለት ነው።
5 .አናሳ እየተባሉ የሚጠቀሱ ነገዶች በልዩ ልዩ ጫናና ደባ ከመዋጥ /ከመሰልቀጥ ይተርፋሉ።
6. የሃይማኖት ተቋማት የሌሎች አገልጋይ ከመሆን አደጋ ተርፈው በየፊናቸው የሚያመልኩትን አምላክ የሚያገለግሉ ይሆናሉ።
7. የልጅ ልጆቻችን በሞራል ስብራታችን ከመሳቀቅና ከማፈር ይተርፉልናል።እንደሚከተለው ከማለት ይሰወራሉ ለማለት ነው።
<< -ሰው እንደ እንስሳ ሲታረድ፣ቆዳው ሲገፈፍ፣የአካል ክፍል በአዋዜ እየተጠቀሰ ሲበላ
-እናትና እህት ስትደፈር፣
-ርጉዝ እህቱ ማኅጸኗ በስለት ተቀዶ ጽንሷ ሲጣል፣
-ሕጻኗ ልጅ “ ወላሂ ዳግመኛ ዐማራ አልሆንም አትግደሉኝ ብላ እየለመነች ስትገደል
-የወገኑ ቤት በላዩ ላይ ሲፈርስበትና በግፍ ሲፈናቀል
መንግሥት እያየ መፍትሔ ሳይሰጥ ሲቀር፣ እንዳውም ተባባሪ ሲመስል ሕዝብ የት ሄዶ ነበር?
እነዚህን ነገሮች እንዴት አልተጠየፈም?
በተቃውሞስ እንዴት ምድርን አላንቀጠቀጠም?
እንደዚያ ኅላፊነት የጎደለው መንግሥት ሥልጣን ላይ እንዲቆይስ እንዴት ፈቀደ?
ትከሻውስ ጭቆናን እንዴት ቢለምደው ነው >> ብለው አይሳቀቁብንም፥ አያፍሩብንም ፥አይታዘቡንም ለማለት ነው።
8.የዐማራን ሕዝብ የሚወጉት ቢያሸንፉ “ፍጻሜው ዘዴውን ያቆነጀዋል” በሚል ፈሊጥ ( the end justifies the means ለማለት ነው) ያደረጉት ግፍ ሁሉ ትክክል እንደነበረ ተደርጎ ይተረካል። ፋኖ ቢያሸንፍ ግን እንደዚያ አይተረክም (ከተሳሳተ ትርክት አንድዬ ይጠብቀን)።
አዎ ፋኖ ቢያሸንፍ “አንቺም ትሞቺብኝ ይሆን ወይ?” ለሚባል አስተዳደር ተጠርቅሞ የነበረው መዝጊያ ወለል ብሎ ይከፈታል። ስለዚህ የአብርሃም አምላክና አምላኩ እንዲያሸንፍ ይርዳው። እናንተም እንጂ! አሜን!
ማስታወሻ፡፡
ከልጅነት እስከ ዕውቀት ዕድሜዬ ጦሱን ስላየሁና ስለሰማሁ ጦርነትን አልደግፍም። እዚህ ሳይደረስ በፊት የዐማራ ሰቆቃ መፍትሔ አግኝቶ ቢሆንና ጦርነቱ ባይጀመር ኖሮ እጅግ መልካም በሆነ ነበር። አሁንም ቢሆን የዐማራ ሕዝብና ዎገኖቹ ጥያቄ መልስ አግኝቶ ጦርነቱ ቢቆም እወዳለሁ።
Comments
Post a Comment